Thursday, September 28, 2023

እንኳን ለመሰቀል በዓል እና መዉሊድም በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን‼️
ዛሬ መስቀልም ነው፣ መዉሊድም ነው።

እንኳን አደረሳችሁ!

ለተለያችሁን ጀግኖችም ሆናችሁ ሌሎች ዘመዶቻችን፣ ነፍስ ይማር።

ሳይነኳችሁ ለነካችሁ፣ ሳያባርሯችሁ ለምታሳድዱን፣

በትግስት ሲተዋችሁ በትእቢት ለተሳደባችሁ፣

አላህ ይፍረዳችሁ! ወዳጃችሁ ጋኔል ያባርራችሁ!

የሰላም ጉዞን ለአሰባችሁ እግዜር ይርዳችሁ።

“ጦርነትም ያልፋል። ስለዚህ የመልሶ መቋቋም የሰላም ጉዞ መጀመር ያለበት አሁን ነው።”

በፈለገው ምክንያታዊነት፣ በማንኛውም መመዘኛ ጦርነት ለሰው ልጅ ስቃይ፣ ህይወት መጥፋት እና ውድመት ያደርሳል እንጅ ዘላቂ፣ ስር ነቀል መፍትሔ አያመጣም። ምንም እንኳን አረመኔዎች ባለን ጉልበተኛነት በጦር ኃይል፣ በመግደል ከፍ እንላለን ብለው ሒሳባቸውን ቢያሰሉም፣ ድንቁርናቸው የሚያስከትለውን መዘዝ፣ የረጅም ጊዜ መከራ ከሰው ልጅ  የመተንበይ ግምት ውጭ መሆናቸውን አይተናል። የዘመናት የግጭት ሰንሰለት እንደሚወልድም አይተናል።

ስለዚህ ግጭቶች በሰላማዊ መንገድ በድርድር፣ በዲፕሎማሲ፣ በውይይት፣ በሽምግልና መፈታት አለባቸው።

ቢሆንም፣ የፓሲፊስት ሰማዕታት አመለካከት እንዳለ ሆኖ፣ በጉልበት ብቻ የምፈቱ ግጭቶች በጣም ጥቂት ቢሆኑም አሉ። ብዙውን ጊዜ ጽንፈኛነትንና የተለዩ ሁኔታዎችን ያመለክታሉ። ይህ የመጨረሻ የጦርነት ግዴታ በከፍተኛ ጥንቃቄ እና በአለም አቀፍ ህግ መሰረት መተግበር አለበት። አሳዛኙ ጉዳይ ግን በሰላም መፍታት ያልተቻለው ግጭት መነሻውና ተንኳሹ ሥልጣኔና ሰብዓዊነት የጎደለው ባለግዜ ወይም ደንቆሮ ፅንፈኛ ስለሚሆን ጦርነቱም አስከፊና ሕግም ሆነ ሰባዊነት የጎደለው ይሆናል። ሰላማዊ ሰው መግደል፣ ባጠቃላይ በሴቶችና በሕጻናት ላይ የሚደረገው እንስሳነት፣  አዝርዕትና እንሥሣትን ማቃጠል፣ የገደሉትን መስቀል፣ መቆራረጥ፣ የአረመኔው ጠባይ ነው። ይህንን እያዩ አሸንፈን ቀን ይወጣልናል የሚሉ መሪዎችም ሆኑ ጀሌዎች የአዕምሮ ዝገት ወይ ሻጋታ አለባቸው።

ለሁሉም ጊዜ አለው። ሁኔታዎች ሲንከባለሉ መጥተው፣ የሽምግልና ጊዜ ከሽፎ፣ በትዕግሥት "ከኔ ይቅር፣ ይሁንልህም" ታልፎ፣  አይቀሬው የጦርነት እልቂት ከተጀመረ በኋላ፣ የታመቀ ቁጭት፣ ትኩስ የበደል ቁስል፣ የምያቅለሸልሽ ትዕቢት፣ የሚዘገንን አረመኔንት እየታዬ፣ የእርቅና የሰላም ጥሪ ቦታ አይኖረዉም። በሳጥናኤልና በጊዮርጊስ መካከል እርቅ አይኖርም። ሳጥናኤል ወደገሃነም ካልተላከ በደልና ጦርነት ዘለዓለማዊ ይሆናሉ። የህዋህትን ጉዳይ አየነው አይደለም?

ይህም ሆኖ በርግጥ ጦርነት አንድ ቀን ማቆሙ አይቀርም። የዚያን ጊዜ ለምያስፈልገው ሰላም፣ ለምያስፈለገው ወደ ሰብዓዊነት የመልስ ጉዞ፣ ጉልበትን፣ ንብረትን ማሰባሰብ፣ ያ የሰላም ጥሩ ተልኮ ይሆናል። መጀመር ያለበትም ዛሬ ነው፣ አሁን ነው! የጦርነት ዕብደት አልቆ፣ ሳያዉቅም በድንቁርና፣ እያወቀም ለሆዱ ሲል የበደለ፣ የገደለ ሁሉ መስከን ሲጀምር አንዳንዱ ጥፋቱ ይገባው ይሆናል፤ ይጸጸትም ይሆናል፤ ከጀሌው ውስጥ ማሩኝ የምልም አይጠፋም። ኢትዮጵያዉያን ያንን የሚያስተናግድ ቄስም፣ ዳኛም፣ ሐኪምም፣ ቴራፔውትም፣ መሃንድስም ያስፈለገናል። አሻፈረኝ፣ አላጠፋሁም የሚለውም በወንጀሉ ሲፈረድበት፣ ሰው ነውና ቅጣቱ በአሸናፊው ሌላ ኢሰብአዊ በደል እንዳይፈጠርበት ያኔ ገለልተኛ የሰላም ልኡካን ያስፈልጉናል። በድህነት የማቀቀች አገር የኋሊት ስትሄድ ቢያንስ ወደ ዜሮ የሚያመጣት ኃይል ያስፈልጋታል። ያ ጉልበት ደግሞ በጦርነት ማቆም ማግስት ከሰማይ አይወርድም፤ ከዛሬው መታነጽ፣ መሰልጠን፣ መሰብሰብ፣ መዘጋጀት አለበት። ጊዜ ይቃጠላል፣  ማለትም የድህነት ሞት የባሰ ይከፋል።

ጦርነትም ያልፋል። ስለዚህ የመልሶ መቋቋም የሰላም ጉዞ መጀመር ያለበት አሁን ነው። ለሰላም የተነሳችሁ ወገኖች ጉልበታችሁ በከንቱ እንዳይባክን ወደዝያ ብታዞሩት?

አላህ/እግዚአብሔር  ይችን ያህል አርቀን ማሰብ እንድንችል ሩህ ለግሶን ይሆን?

 

መልካም መውሊድ! መልካም መስቀል!

Yeshiwork Wondmeneh 
https://amharic-zehabesha.com/archives/186124

No comments:

Post a Comment

https://youtu.be/VUfa5eupQTc?si=Zm73w18dFB27xlqD       https://youtu.be/LcFmz2Xq5MY?si=7uP6VZsd2ksEulUf   https://youtu.be/7dUVmj8go7s?si=Px...