Wednesday, June 28, 2023

መርዶ በሞንታርቦ፡ የህወኃት ትሩፋት - በደሳለኝ ቢራራ
የህወኃትን የጭካኔ ልክ ቃላት ከሚገልጹት በላይ የአካል ማስረጃዎችና ሰለባ የተደረጉ ሰዎች ምስክርነት ተደርጓል። በታሳሪ አፍንጫ እስክርቢቶ በመኮርኮር መረጃ አውጣ ከማለት እስከ ጥፍር መንቀልና ብልት ላይ ማንጠልጠል በበርካታ አማራ ተወላጆች ላይ ተፈጽሟል። ህወኃት ጸረ-አማራ አይዲዮሎጅ ይዞ እንደተነሳ ድርጅት አማራን ማሰር፥ መግደልና ማሳደድ በስውርም ሆነ በይፋ ሲፈጽመው እንደ መደበኛ ስራ ተቆጥሮ የኖረ ስቃይ ነበር። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እየተስተዋለ እንደመጣው ግን የትግራይ ህዝብንም ቢሆን በዲሞክራሲ መንገድ ስልጣን ይዘናል ለማለት ያህል “የምንወክለው ትግራይን ነው” ለማለት ያህል ይጠቀሙበታል እንጅ በመሰረታዊነት ህወኃት ለትግሬም ቢሆን ደንታ እንደሌለው በገሀድ መታየት ጀምሯል።

እስከዛሬ የሚታወቀው የህወኃትና የትግራይ ህዝብ ትስስር ‘ወያነ’ በሚል የጋራ እሴት ‘ህወኃት ትግራይ ነው፡ ትግራይም ህወኃት ነች’ በሚል ፍጹም አንድ መሆንን በሚያስረዳ መስተጋብር ይገለጽ ነበር። በህወኃት ተደጋጋሚ ስልጠናዎች የሰረጸ “ትግራይ ከሌለች ህወኃት የለም፤ ህወኃትም ከሌለች ትግራይ የለችም!” የሚል ጥልቅና አስፈሪ ትስስር ተሰርቷል። በመሆኑም የትግራይ ህዝብ ህወኃትን የሚያምንና በህወኃት የሚተማመን፥ ህወኃት አድርግ ያለውን ሁሉ ለማድረግ የማያቅማማ እንደሆነ በተለያዩ አጋጣሚዎች ተረድተነዋል። ለምሳሌ፡ በሚሊየን የሚቆጠር የትግራይ ህዝብ የህወኃትን ጥሪ ተቀብሎ ሰሜን ወሎን፥ ዋግኸምራን፥ ደቡብ ወሎንና ደቡብ ጎንደርን ወረራ ሲፈጽም በከፍተኛ የጥላቻ በቀል የህዝብ ተቋማትን በማውደምና የግል ንብረቶችን በመዝረፍ ነው። የትግራይ ህዝብ የፈጸመውን ይህንን ወንጀል ለፖለቲካ ትክክልነት ብዬ በህወኃት ስም ብቻ አልሸበልለውም። ህወኃት የነበረው አጠቃላይ ምሊሻ፥ ልዩ ኃይልና ፖሊስ ተደምሮ 250 000 ገደማ ነው። አማራን የወረረው ግን እስከ ሁለት ሚሊዮን የሚደርስ (ምናልባትም አቅም የፈቀደለት የትግራይ ተወላጅ በሙሉ) በመዝመት ነው። የፓርቲ አባል ያልነበረ፥ ወታደር ያልሆነ፥ ምንም አይነት የፖለቲካ ተሳትፎና ፍላጎት የሌለው የህብረተሰብ ክፍል በጅምላ ተነስቶ አጎራባች ህዝብን ለመውረር ከዘመተ የማስተባበር ስራ የሰራው ድርጅት ብቻውን ተወቃሽና ተከሳሽ የሚደረግበት ምክንያት የለም።

ህዝቡ የተጋተውን የጥላቻ ፕሮፓጋንዳ ሰምቶ ከነባር ባህልና አስተሳሰቡ ውጭ የሆኑ ዘግናኝ ነውሮችን ፈጽሟል። መነኮሳትን ማስነወር፥ ዱዳ እንስሳትን መጨፍጨፍና የእንጀራ መሶብ ላይ መጸዳዳት የትግሬ ማህበራዊ አኗኗር እና ባህል መገለጫ አልነበረም። ባሳለፍነው ጦርነት የትግራይ ህዝብ ይህንን ነውር ነው የፈጸመው። ወንድማማችነትና ሰላም የሚናፍቃቸው ወገኖች እንደዚህ አይነቱን ሀቅ በዝርዝር እንዲነሳ አይፈልጉትም፤ ተድበስብሶና ወደ አንድ በጋራ የምናጥላላው አካል ተላኮ ህዝቡን ብጹዕ ማድረግ ነው የሚፈልጉት። ዳሩ ግን በውሸት ከሚመጣ ሰላምና ወንድማማችነት ይልቅ በቂም ተይዞ የሚዘገይ ፍትህ ይሻላል። አንድ ህዝብ በሌላ ህዝብ ላይ ላደረሰው በደል ህዝባዊ ፍትህ እና እርቅ ሳይደረግ የግል ጥቅምባሰገራቸውና የስልጣን ጥማት ባንገበገባቸው ፖለቲከኞች ተምታትቶ እንዲቀር ቢደረግ ጊዜውን ጠብቆ የሚነሳ የፍትህ ታጋይ ኃይልን ቀብሮ ማሳደር ነው የሚሆነው። እውነተኛ ፍትህና እርቅ ግን ዘላቂ ሰላምና አስተማማኝ ወገንነት እንዲኖር ያደርጋል። ያሳለፍነው ጦርነት በምንም ሁኔታ ቢቋጭ ከህዝቡ የሚቀረውን እዳ ሳልጠቁም ማለፍ ስለማልፈልግ ነው ይህን ያነሳሁት። በዋናነት ግን በዚህ አጭር ጽሑፍ ለማውሳት የምወደው ‘ህወኃት ስለትግራይ ህዝብ ምን ያስባል?’ ስለሚል ጥያቄ ነው።

የትግራይ ህዝብ “ሀዘኑ ሀዘኔ፤ ደስታውም ደስታዬ፤ ጥቅሙን ማስከበር አላማዬ፤ ክብሩ እሴቴ . . . ነው” ይላል? መሬት ላይ ከምናየው እውነታ እንደምንረዳው ህወኃት ለትግራይ፡ ብአዴን ለአማራ ህዝብ ከሆነው የተለየ ሁኖ አይታየኝም። ልዩነቱ ህወኃት በትግራይ ይወደዳል ፤ ብአዴን ግን በአማራው ዘንድ ይጠላል ብቻ ሳይሆን ‘የአማራ ህዝብ ብአዴንን ይጠየፈዋል’። ምክንያቱም ብአዴን ምንም ከአማራ ህዝብ ጋር የሚነካካ ነገር የሌለው ፍጹም ቆሻሻ የሆነ ስብስብ ነው። ብአዴን የሚያደርጋቸውን ማናቸውንም እንቅስቃሴዎች የአማራ ህዝብ በዐይነቁራኛ ነው የሚያያቸው፤ ምክንያቱም ባንዳ ከሀዲ፥ አድርባይና ተላላኪ የደናቁርት ስብስብ መሆናቸውን ህዝቡ ያውቃል።

ህወኃት ግን በግልጽ በመንግስታዊ አቋም ደረጃ “ሁለት ሚሊዮን ትግራዋይ ሰውተን ወደ ስልጣናችን መመለስ ከቻልን ጥሩ ነው” የሚል መግለጫ ሲሰጥ ህዝቡ “እንበር ተጋዳላይ!” እያለ በዘፈን ተቀብሎታል። የትግራይ ህዝብ ህወኃትን በስልጣን ለማቆየት ለመሰዋት ፈቃዱን የሰጠው እራሱ ነው። አስቀድሞ ህወኃት አቋሙን ሲገልጽ ህዝቡ መልስ መስጠት ይችል ነበር። ቢያንስ ቢያንስ “እናንተን በስልጣን ለማቆየት አይደለም የምንሰዋው፤ ትግራይን ነጻ ለማውጣት አላማ አድርጋችሁ ከታገላችሁ በኋላ በስልጣን ሰላሳ ዓመት ኖራችኋል፤ አላማችሁን የት አደረሳችሁ?” ብሎ መጠየቅ ይጠበቅበት ነበር። ህዝቡ ግን ከመጠየቅ ይልቅ ማገዶ ለመሆን ነበር የተዘጋጀው። ተማገደ አለቀ። በዚህም ብቻ በበቃ።

ህወኃትን በነበረው ማንነት በጣሳቸው ህጎችና ባሉበት በርካታ ተጠያቂነቶች ምክንያት ከፓርቲነት የሰረዘችውን የምርጫ ቦርድ ኃላፊ ወ/ር ብርቱካን ሚደቅሳ ስልጣን እንድትለቅ መደረጉን ሪፖርተር ጋዜጣ ሰኔ 18 ቀን 2015 በወጣው እትሙ አትቷል። ተሰርዞ የነበረው “የህወኃት ህጋዊ ሰውነት እንደገና እንዲመለስ መጀመሩ. . . “ ይላል ርዕሱ። ህወኃት ወደ አንድ ሚሊዮን የሚጠጋ የትግራይን ህዝብ ጨፍጭፎ በመጨረሻም የኦነግ ተለጣፊ ሁኗል። አሁን ህወኃት ከኦነግ ጋር የጫጉላ ሽርሽር ላይ ነች። በትልልቅ ሞንታርቦ አዲስ አበባ ላይ “በሎም!” እየተባለ በውስኪ እጅ እየታጠቡ ነው።

ታዲያ ስልሳ አመት በነጻ አውጭነት ብራንድ፥ ሰላሳ አመት በስልጣን የኖረውን ህወኃት “ወያናይ መስመርና፡ አፈር ልሰን ተነሳና” ማለት የትግራይን ህዝብ ንቃተ ህሊና አያስጠይቅም? አሁንስ የትግራይ ህዝብ የተገለጸለት ነገር ይኖር ይሆን? ህዝባዊ አንድምታውስ በምን ምልክት ወይም ድርጊት ሊገለጽ ይችላል? ከሁሉም ነገር በበለጠ የሚገርመው ደግሞ ህወኃት በዚህ ጦርነት ሰለባ ያስደረጋቸውን የህዝቡ አካላት ለቤተሰባቸው መርዶ ያደረገበት መንገድ ነው። የሟቾችን መርዶ እንደ ህዝባዊ በኣላት ወይም እንደ ሰርግ ትልልቅ ሞንታርቦዎችን ሰቅሎ እንደ ሜዳሊያ ተሸላሚ የሟቹን ስም እየጠራ፡ የሟች ቤተሰብ በድንጋጤና በለቅሶ ሲንፈራፈር ገመናውን ቪዲዮ ቀረጻ እያደረገ ነው። በአማራ ልማዳዊ አገላለጽ እጅግ የከፋ ነገር ሲያጋጥመን “አረ ለጠላቴም አይስጠው” እንላለን። እንደዚህ አይነቱን ለማለት ነው።

 

ፎቶ፡ https://twitter.com/KeyAstra/status/1673400818806956047/video/1
https://amharic-zehabesha.com/archives/184184

No comments:

Post a Comment

https://youtu.be/VUfa5eupQTc?si=Zm73w18dFB27xlqD       https://youtu.be/LcFmz2Xq5MY?si=7uP6VZsd2ksEulUf   https://youtu.be/7dUVmj8go7s?si=Px...