Thursday, June 29, 2023

ወልቃይት ፣ ጠለምት እና ራያ ህወሃት በከለለው ግዛት ስር ይሁን ፣ (Status- Quo -Ante) ይከበር የሚለው ቅዥት እና ተረት ተረት
መግቢያ

እንግዲህ ግራ የተጋባ ፣ በሕግ የማይመራና ራሱን በተንኮል የተበተበ መንግስት እና ፓርቲ መዘባረቅ ፣ ሕዝብን ማደናበር እና የማይጨበጥ አካሄድ መከተል እና ተረት ተረት ማብዛት ስራው ነው።

የወልቃይት ፣ ጠለምት እና ራያ ወደነበረበት አስተዳደር ይመለስ ሲባል ከመነሻው ማነው ያለአግባብ ፣ በማንአለብኝነት እና በኃይል  እነዚህን ግዛቶች ወደራሱ ግዛት ያጠቃለለው የሚል ጥያቄ ሲነሳ መልሱ በማያሻማ መልኩ “ህወሃት” የሚባል አጉራ ዘለል ፖርቲ መሆኑ የማይታበል ሃቅ ነው።

ይህን መነሻ አድርገን በያዝነው 19ኛው ምዕተ ዓመት የተከሰተን ታሪክ/Contemporary History/ ስናይ የአርጀንቲና መንግስት በእንግሊዝ አስተዳደር ስር የነበረችውን ፎክላንድ (The  Falkland Islands) ደሴት በጉልበት እና በኃይል ያዘ።

ደሴቲቷን የእንግሊዝ መንግስት ከመነሻው በአግባብ ነው ወይ ወሮ  የያዘው ? የሚለው አመክንዮ አጠያያቂ ቢመስልም አርጀቲና ግን ሕጋዊ መዓቀፍ ተከትላ ቦታውን ስላልያዘችው የእንግሊዝ መንግስት “አርጀንቲና ሆይ ግዛቴን ልቀቂ/ (Status Quo Ante ) ይጠበቅልኝ ብላ ጠየቀች።

አርጀንቲናም “ በደንበሬ ጥግ የሚገኝ ግዛቴ ነውና አለቅም” ብላ አሻፈረኝ አለች።

ከዚያ የእንግሊዝ መንግስት በኃይል ሆነ በዲፕሎማሲ አግባብነት ባለው መልኩ ደሴቷን መልሶ በቁጥጥር ስር አዋለ።

ይህን መሰረት አርገን የወልቃይት ፣ ጠለምት እና ራያን ጉዳይ ስናይ ገና ከጅምሩ እንደ ኢትዮጵያ አቆጣጠር በዚህ የትውልድ የታሪክ ዘመን በ1984ዓ.ም. አካባቢ (Contemporary History) በአፍሪካ ታሪክ ታይቶ በማይታውቅ አኳሃን በአንድ አገር ክልል ያለን ግዛት በኃይል ቆርሶ እና (Annexed ) አድርጎ የያዘ አጉራ ዘለል ፓርቲ ቢኖር “ህወሃት” የሚባል ዘረኛ ፓርቲ ነው።

ይህን በመቃወም የወልቃይት ፣ ጠለምት እና ራያ አባቶች ተቃወሙ ። ወልቃይት ፣ ጠለምት ፣ ራያ ወደነበረበት ግዛት ይመለስ ( Status Quo Ante) ይጠበቅ  ብለው ጠየቁ ። ህውሃት ግን “ ጀሮ ዳባ ልበስ” ብሎ እንደ አርጀንቲና “እሻፈረኝ “ አለ።

ጊዜው ደረሰ እና የወልቃይት ፣ ጠለምት እና ራያ ነፃ አውጭ ጀግኖች ከ 27 ዓመት ቆራጥ ተጋድሎ በኋላ እርስታቸውን እንደ እንግሊዝ ግዛት ፎክላንድ ደሴት (Falkland Islands ) ግዛታቸውን በደም እና በአጥንት መስዋእትነት አስመለሱ።

በአንድ አካባቢ ግዛት ስር የነበረን እርስት ወደነበረበት ህግን ወይም ኃይልን ተጠቅሞ የማስመለስ አካሄድ (Status Quo Ante) ይሉሃል ይሄ ነው። አለቀ ደቀቀ ህግን ተክትሎ ለሃያ ሰባት ዓመት ወልቃይት፣ ጠለምት እና ራያ ወደነበሩበት ቦታ እንዲመለሱ መላው የአማራ ሕዝብ ጠየቀ ፣ ምላሽ ሲታጣ አሻፈረኝ ያለን ኃይል በሚገባው ቋንቋ ተነግሮት ጥያቄው እልባት አግኝቷል እንላለን።

ሌላው መላው ኢትዮጵያዊ ሊረዳው የሚያስፈልገው ጉዳይ ኦነግ /OLF/ እና ህውሃት /TPLF/ ከማን ነፃ እንደሚወጡ ግራ የሚያጋባ ቢሆንም “ነፃነታችን እንሻለን” ብለው መታገል ከጀመሩ ሃምሳ  ዓመታት በላይ ሊሆናቸው በእጣት የሚቆጠሩ ዓመታት ቀርቷቸዋል ። “ምን አይታ ዶሮ ምን አደረገች” እንዲሉ ይህ የነፃነት መሻት ዳርዳርታቸው ያቆጠቆጠው ከኤርትራ ነፃነት ግንባር ጥያቄ ማግስት ከራርሞ እንደሆነ ለማንም ግልፅ ነው።

የኤርትራ የነፃነት ጥያቄ “አግባብ ነው አግባብ አይደለም” የሚለው ጥያቄ እንዳለ ሆኖ እና መሰረታዊ ምክንያቶች ቢኖሩም ዛሬ “ኢትዮጵያ” ብለን የሚንጠራትን ሃገር ኤርትራውያን “አቢሲኒያ” ብለው ለመጥራት የሚቀናቸው ሕዝቦች መሆናቸው ጥርጥር የለውም።

የሚገርመው ደግሞ “ህውህት” እና “ኦነግ ብልፅግና” የመገንጠል እና የነፃነት ጥያቄ አባዚያቸው ይታገስላቸው ይሆናል በሚል ህሳቤ የሃገረ መንግስትነት ሥልጣን ጀባ ቢባሉም አደናገሩን ፣ ግራ አጋቡን እና “ከድጡ ወደ ማጡ” ወሰድን ።

“ነገሩ ወዲህ ነው” እና “ ሲከፋሽ ወደ እኔ ሲመችሽ ወደ እሱ” እንዳለው ዘፋኙ “ከእኛ በላይ ኢትዮጵያዊነት ለአሳር” ፣ “ኢትዮጵያ አትፈርስም ወ.ዘ.ተ. ገለመሌ ፣ ገለመሌ ፣ ያደበሌ “ የሚሉውን ነጠላ ዜማቸውን ደረደሩልን ግራሞትን ፈጠረብን እና “አጃየብ” አልን።

የሚገርመው ስልጣን ከያዙ በኋላም ቢሆን ከህሊናቸው እና ከአቋማቸው ገሸሽ የማይለው ጥዮፍ ባህሪያቸው እና  የቂመኝነት ትርክታቸው እነ “ህወሃት” እና “የኦነግ ብልፅግና” “ከሃገሬ ኢትዮጵያ በፊት እኔን” የሚሉትን የአማራ እና መሰል ብሔር ብሔረሰብ ሕዝቦችን ማሰቃየታቸውን ፣ ማሰራቸውን ፣ መግደላቸውን እና እንደ ጠላት አርገው መፈረጃቸውን ቀጥለውበታል።

ይህን የከረፋ ድርጊታቸውን በ27 ዓመታት የህወሃት እና በአለፉት አምስት ዓመታት የመከራ ፣ የግፍ ፣ የዘረኝነት እና ፅንፍ የረገጠ የኦነግ ብልፅግና አካሄድ ላይ አይተንዋል።

የኤርትራ ፣ የትግራይ ምድር ቀይ ባህርን ይዞ (የሳባ ምድር)፣ ( የከለው ምድር) (ወልቃይት ፣ ጠገዴ ፣ ጠለምት ፣ ጎንደር ፣ ጎጃም ፣ አማራ ሳይንት ፣ ቡግና ፣ የሽዋ ምድር ፣ ወሎን ይዞ ወ.ዘ.ተ.) ፣ በለው ( ኩናማ ፣ ኢሮብ) ፣ የአፋር እና ከዚህም ከዚያም የተበታተነው “የአገው” የአኩኖ -ወሳባ” ልጆችን አካቶ የሴሜናዊው የኢትዮጵያ  ምድር ተወላጆች ከፍጥረታቸው ጀምሮ  የኢትዮጵያ አስኳል እና መነሻ መሆናቸው የሚታወቅ ነው።

ነገር ግን ጥቂት በቀኝ ገዥ ባንዳ ጡት ስር ያደጉት ህውሃቶች (የሳባ ነገዶች) “ኢትዮጵያዊ አይደለንም” ብሎ መወክሸታቸው እና መጎረራቸው “ዐይንን በጨው ታጥቦ እውነታን እንደመካድ እና “የማያዛልቅ ፀሎት ለቅፅፈት” እንዳይሆንባችሁ” ብለን እንመክራቸዋለን።

ከአኩኖ -ወሳባ ወንድማቾች እና እህታማቾች ከበለው ፣ ከከለው ፣ ከሳባ ነገዶች ባሻገር ከአማራ ወንድሙ ከከለው ጋር እንደተዋሃደው አገው ሁሉ “ላካንዶን” እና “ኖቫ” የሚባሉ ወንድም ነገዶች በሳባ ፣ በከለው እና በበለው ነገድ ተውጠው የቀሩ ነገዶች እንደነበሩ ሊታወቅ ይገባል። ይህ ማለት ምን ማለት ነው? “አገው” ከአማራ ወንድሙ “ከከለው” እና “ከበለው” ጋር ተዛምዶ ፣ተቀላቅሎ እና ተሰባጥሮ ቢኖር ምንም ማለት እንዳልሆነ አስረግጠን እናስረዳለን።

ታሪክ /History/ ፣ /fable/ ተረት ተረት/ እና ዘመኑን የዋጁ ታሪኮች / Contemporary History/ እና አድምታው :

 

በሃገራችን ኢትዮጵያ ባለፉት ሰላሳ ዓመታት እያየነው ፣ እየሰማነው እና እየኖርንበት ያለው ተጨባጭ ሁኔታ በ “ታሪክ (History)  እና ተረት - ተረት (Fable)” መካከል ያለውን ልዮነት ሆንብለው በማፋለስ ፣ በማጣመም ፣ በማደነገር እና በመተብተብ ጥቅማቸውን ለማስጠብቅ የሚሹ ፣ የመስፋፋት ህሳቤ ያላቸው  እና በሥልጣን ኮረቻ ላይ ለመሰንበት የሚውተረተሩ ግለሰቦች ፣ ፖለቲከኞች ፣ መሰሬ ምሁራን  ፣ ተከፋይ የማህበረሰብ አንቂዎች ፣ አፍረተ ቢስ የበይነ-መረብ ባለሙያዎች  ወ.ዘ.ተ.  መላ ሕዝቡን እያደናበሩ ፣ እያምታቱ እና ግራ እያጋቡ ይገኛሉ።

ታሪክ /History/ :

ማለት ያለፉትን ዘመናት እውነታዊ ክሳቴዎች ጠቅለል አርጎ የሚያቀርብ ፣ የሰው ልጅ ከቅድመ አያቶቹ ተላልፈውለት አስታውሶ የሚዘግብበት ፣ ተመራምሮ ያገኝውን ፣ ያወቀውን ዕምቅ ሃሳብ ፣ በውስጡ አመላካች ወካይ ተቋማዊ ማስረጃዎችን አጠናክሮ እና አካቶ በማቅረብ እንዲሁም የክስተቶችን ሃሳባዊ ትርጓሜ ዘርዝሮ የሚያስቀምጥበት የዕውቀት ዘርፍ ነው። “History" is an umbrella term comprising past reliable events as well as the memory, discovery, collection, organization, presentation and interpretation of these events”

ትርክት -ተረት -ተረት- /Fables -Fictives / : ይህ ከእውነታ አዘል ታሪክ የተቃረነ መነባንብ ፣ ተረት የበዛበት ፣ ተናጋሪው ወይም ፀሃፊው የራሱን የይሆናል የግል ማህደር ፅሁፍ ፣ በጥላቻ ተነሳስቶ የሚዘላብደው እና ሰዎች በጋዜጣ ያሰፈሩትን እንቶ ፈንቶ  የያዘ ህተታ ማለት ነው -“ Fables are any chronicle, journal or diary, – thus almost any authored material – is bound to be unreliable since someone has written it (and he will have prejudices and opinions).”

 

ዘመኑን የዋጁ ታሪኮች / Contemporary History:

 

ይህ አይነቱ ታሪክ ደግሞ እንደ አውሮፓውያን እቆጣጠር ከ1946 መባቻ ጀምሮ ፣ ዓለም በጦርነት ታምሳ በነበረችበት ፣ ከቀዝቃዛው ጦርነት መባቻ እና እስከ አሁኑ ዘመን ያሉትን በተለይ በሕይዎት ያለው የዓለም ሕዝብ የኖረበትን ፣ የሚመሰክረውን እና የሚያረጋግጠውን ክስተታው ኩነቶች የሚያካትት ታሪክ ነው። “Contemporary History:  generally defined as beginning in 1946 and continuing to the present. In that time, the world has been almost continuously at war. The Korean War and the Vietnam War existed alongside the Cold War waged between the United States and the Soviet Union.”

 

ዘመኑን የዋጁ ታሪኮች / Contemporary History / : የወልቃይት ፣ የጠለምት እና የራያን ጥያቄ  ሊፈታ የሚያስችል እንድምታ እንዳለው  ስንመረምር :

ይህን መሰረት አድርገን ቀደመት የዓለም ሃገራትን ጆግራፊያዊ አሰፋፈር እና አሁን ያሉበትን የግዛት ይዞታ ስናይ በጣም የሚያስደምም ነገር እናያለን ። አሜሪካ የምትባለው ሃገር በአይርሾች ፣ በእንግሊዞችና በስኮትሾች እጅ ከመውደቋ በፊት የቀዮቹ ህንዳዊያን /Red Indians/ ሃገር ነበረች።  እነካሊፎርኒያ የአሜሪካ ግዛት አልነበሩም ነገር ግን በጦርነት ፣ በወረራ ይሁን በመልካም ፈቃድ አሜሪካ ስፖኒሽ (Spanish) ተናጋሪውን የካሊፎርኒያ ምድር አሜሪካ የራሷ ግዛት አድርጋቸዋለች።

እንግሊዝ አሁን ቦቲ ጫማ የምታከል ሃገር ከመሆኗ በፊት በቀኝ ግዛት ዓለምን ጠቅልላ ውጣ ስለነበር “ፀሃይ በታላቅዋ ብሪታንያ አትጠልቅም /The sun never set in England /” ተብሎ የተዘመረላት ሃገር ነበረች።

ይህን ያመጣሁት ግራ ነፈሰ ቀኝ ከአሁን በኋላ የዓለምን ከ1946 ማለትም በኢትዮጵያ ቀን አቆጣጠር ከ1938 ወዲህ ያለውን ፣ የምናውቀውን ታሪክ ፣ የእኛ አያቶች እና አባቶች  የነገሩንን ፣ የዘመኑ ትውልድ የሚያውቀውን እና የሚመሰክረውን ታሪክ መሰረት አድርገን መሄዱ እንድም ያስታረቃናል ፣ የጥንት ታሪኮችን እውነታ በጥናት አስረግጠን በማጣቀስ የመፍትሄ ሃሳብ ልናቀርብበት እንችላለን።

ይህን የምንጨብጠውን ፣ የምናውቀውን እና እየኖርንበት ያለውን ዘመኑን የዋጀ ታሪክ /Contemporary History/ መሰረት አድርገን እኛ ኢትዮጵያውያንን እያጋጨን ያለውን የመሬት የይገባኛል ጥያቄዎች የጥንት ታሪኮች /Ancient History/ እንዳለ ሆኖ ፣  በቅንነት ፣ ሃገራችን ትዳን ብለን ፣ በወል የጋራ ህሳቤ ፣ በንፁህ ህሊና ፣ ከስግብግብነት ነፃ በመሆን እና በመተማመን ብነጋገር ወደመፍትሄው እንደርሳለን ብለን እንሟገታለን።

የዘመኑን ትውልድ የታሪክ ጭብጥ እና እውነታ (Contemporary History)  አንፃፅረን ስናይ ወልቃይት ፣ ጠለምት እና ራያ በአሁኑ ዘመን ትውልድ እይታ የጎንደር እና የወሎ አማራ ዕርስት መሆናቸው የማይታበል ሃቅ ነው።

 

ቁርጠኝነት የሚጠይቅ ተግባቦታዊ ውሳኔ :

የጋራ ታሪካችን በተመለከተ:

ከ3000 እና ከዚያ በላይ የሆነው የኢትዮጵያዊነት ታሪካችን ሃቅ ስለሆነ፣ በእውነተኛነት ማስረጃ የተደገፈ በመሆኑ እና በጋራ እንደ ሕዝብ  የሚያግባባን ጉዳይ ነውና የህውሃት እና የኦነግ ፅንፈኞችን የሚያደናግር ፣ ያላዋጣንን ፣ ኪሳራ እንጂ ትርፍ ያላስገኘልንን ትርክት /Fable/ አሽቀጥረን በመጣል በጋራ ታሪካችን ላይ ብንግባባ ።

ይህን መሰረት እድርገን ስንሞግት ኢትዮጵያ አለች ፣ ለወደፊቱም ትኖራለች ፣ የጋራ ቤታችን ናትና ተዋደን አንድ ሁነን እንኑርባት ብለን እንመክራለን ።

አዲስ አበባን : በተመለከተ የኢትዮጵያ ዋና ከተማ ከመሆኗ በፊት የተለያየ ስም እየተሰጣት ብትዘልቅም እወነታዊው የኢትዮጵያ ዋና ከተማ ታሪኳ እየገነነ የመጣው በዚህ ትውልድ ታሪክ (Contemporary History) በምንለው ወቅት ከጎንደር የኢትዮጵያ ዋና ከተማነት ቀጥላ የተፀነሰች ከተማ በመሆኗ እና የከተማነት ገፅታ ያላበሷትም መላ ኢትዮጵያውያን በመሆናቸው አዲስ አበባ “የኢትዮጵያ እና የመላ ህዝቦቿ ዋና ከተማ ናት” የሚለው አካሄድ ያስማማናል።

ነገር ግን ብልጡ እና ዐይነ አውጣው “ህወሃት” ለኦነግ “አዲስ አበባ የኦሮሞ ናት ብየ እንደ ማሞ ቂሎ ብሸነግልው ፣ ወልቃይት እና ራያን የህወሃት ትግራይ ናት” ብሎ ከጎኔ ይቆማል እና ይከራከርልኛ የሚለውን “ የአይጥ ምስክሯ ድንቢጥ” የሚለውን አካሄዱ ገሸሽ አድርጎ በእራሱ ጥፋት የተሰውበትን ከአንድ ሚሊዮን በላይ ሕዝቦችን ወላጆች ቢያፅናና እና አካለ ስንኩል የሆኑትን እንዲያገግሙ ቢረባረብ እና በኢትዮጵያ የጋራ የሃገር ግንባታ ሂደት ላይ ቢያተኩር የሚዋጣ ይሆናል እንላለን።

ወልቃይት ፣ ጠለምት እና ራያን በተመለከተ ፣

ታሪክን ወደ ኋላ ጎተት አድርገን ስናይ ከአኩኖወሳብ ልጆች መካከል አንዱ የሆነው “የሳባ” ልጆች ነገድ ቀይ ባህርን ይዞ ከተከዜ ተሻግሮ ባለው ምድር ያለትን ሕዝቦች ከኩናማው ፣ ከአፋሩ ፣ ከኢሮቡ ወ.ዘ.ተ. ነገዶች ሌላ ያሉትን ሕዝቦች ያጠቃልላል ።

ከተከዜ ወዲህ ያለ ምድር የአኩኖወሳባ” ልጆች “የከለው” የአማራ እና በከፊል “የበለው” ልጆች ምድር መሆኑን ረጅሙ የኢትዮጵያ የታሪክ እውነታ አስረግጦ ይናገራል።

ይህን ጥንታዊ ታሪክ ለጊዜው ተግ እናድርገው እና የአሁኑን ትውልድ ታሪክ (Contemporary History) ማለትም ከ1938 ዓ.ም. ወዲህ ያለውን ሃቅ አዘል የሆነውን ታሪክ ተመርኩዘን ስናይ ወልቃይት ፣ ጠለምት በጎንደር ክፍለ ሃገር ፣ ራያ በወሎ ክፍለ ሃገር ስር ሁኖ ይትዳደር የነበር መሆኑ የማይታበል ሃቅ ነው።

እንግዲህ በጥንት ዘመን የነበሩ ቅድመ አያቶቻቸን እና ምንዥላቶቻችን ከሞት ተነስተው ለመመስከር ስለማይችሉ እና በሕግ እያታም ለምስክርነት ስለማይበቁ ፣ የቁም ምስክሮች ፣ የዚህ ዘመን ያሉ የታሪክ ውጤቶችን እና ጭብጦች በመሆናቸው ወልቃይት ፣ ጠለምት እና ራያ አሁን ባሉበት የአማራ ክልል ተካለው መዝለቃቸው የግድ የሚላቸው ይሆናል እንላለን።

ማጠቃለያ :

እንደዚህ አይነት በሆደ ሰፊነት የሚሰጥን ሃሳብ መግዛት “ምከረው ፣ ምከረው ካልሆነ መከራ ይምከረው” እንዲሉ ፣ በዚህ በያዝነው ትውልድ ዘመን የሞትን ፣ የመፈናቀልን ፣ የኢኮኖሚ ድቀት እና ስደትን  የትግራይ ሆነ የኦሮሞ ሕዝብ በሚገባ ይገነዘበዋል ተብሎ ስለሚታሰብ ከወዲሁ የሚበጀውን ያደርጉ ዘንድ ምክራችን እንለግሳለን።

ይህ ሆኖ እያለ ሰሞኑን የህውሃት እና የብልፅግና ተከፋይ ማህበራዊ አንቂዎች ፣ ቲክ ቶከሮች (Tiktokers) እና ዮቲዮበርስ በተፈጥሮ የሌለበትን የአማራ ነገድ “ተስፋፊ” ፣ ወልቃይት ፣ ጠለምት እና ራያ የሌለ ተረት ተረት (Fable) እያነበነቡ  “በታሪክ የትግራይ” ነው ፣ “27 ዓመት በነበረበት ግዛት ስር ይሁን” እና “ (Status Quo Ante )” ይከበር እያሉ እየለፈፉ ማህበረሰቡ ወደ እማያባራ ጦርነት እንዲገባ ተግተው በመስራት ላይ ስለሆኑ ይህን ፅሁፍ በመከተል የሚመለከተው አካል ስራውን ቢሰራ ያዋጣል ፣ ሕዝብ እርስ በርሱ እንዳይፋጅ ይረዳል እንላለን።

በእልህ ፣ በስሜት በእውሸት ትርክት ተነሳስቶ እና በሌላው ስር ተወትፎ “  ከወሬ ያልዘለል ትርክት እየተረኩ ከእውነታ ውጭ የሆነ አጃንዳን አሳካለሁ ብሎ መወላገድ ትርፉ እልቂት ይጋብዛል እንላለን።

 

ተዘራ አሰጉ

ከምድረ እንግሊዝ።

 

 
https://amharic-zehabesha.com/archives/184215

No comments:

Post a Comment

https://youtu.be/VUfa5eupQTc?si=Zm73w18dFB27xlqD       https://youtu.be/LcFmz2Xq5MY?si=7uP6VZsd2ksEulUf   https://youtu.be/7dUVmj8go7s?si=Px...