Sunday, April 23, 2023

የአማራ ማዘናጊያ ቁማሮች አያልቁም፡-ትናንት ኢትዮጵያ ዛሬ ደሞ ሰላም!
በላይነህ አባተ (abatebelai@yahoo.com)

#image_title

አማራን ለዘር ፍጅት የዳረገው ሃይማኖትም ሆነ ባህል የሌላቸው አረመኔዎች፣ ጭራቆች፣ ቀጣፊዎችና የዘራፊዎች ቁማር ሰለባ መሆኑ ነው፡፡  ከተናንት ወዲያና ትናንት ኢትዮጵያና አባይን ታንገት በላይ እየዘፈኑ ስንቱን አጃጃሉ፡፡ ዛሬ ደግሞ የማያውቁትን ሰላም እየዘፈኑ የቀረውን አማራ እርስት አልባ ለማድረግና ከቻሉም ለማጥፋት የሰላም ቁማርን እየተጫወቱ ነው፡፡

ለሶስት ሺህ ዘመናት ሳይሳካላቸው የቀረውን የምእራባውያን የዘር ካርታ እያነበበ አማራን እርስቱን ያስወረሰው ለገሰ ዜናዊ በወቅቱ በነበረው ያረቦች አመፅ መክንያት በእስራኤሎችና በምዕራባውያን ትዕዛዝ እንደዚሁም ሲወለድ በተነቀረበት የአማራ ጥላቻ የአማራን ጥቅም ለመንጠቅ ዓባይን ተሱዳን ደጃፍ ሊገድብ "ሕዳሴና ቦንድ" እያለ ቃዠ፡፡ የለገሰ ቅዥት እንደ ዛር ተኮፍሷቸው የሰይጣን ቁራጩ ለገሰ ቦንድ እንዲሳካ ስንቶች "ምሁራን" ስንክሳር እሚያካክል ጥሑፍ ጣፉ፡፡ ስንቶች ሆዳም ካድሬዎች የቦንድ ስብሰባዎችን ለማዘጋጀት መቀመጫቸውን አማቱ፡፡ ስንቶች በሕዝባቸው መቃብር እንጀራ እሚጋግሩ ዘፋኞች ልማት፣ ህዳሴና ታድሶ እያሉ ዘፈኑ፡፡ በእነዚህ ህሊና ቢስ ጉዶች ተላላኪነት የተሰበሰበው የቦንድ ገንዘብ ወገኖቻችውን እንደ ደን ከማስጨፍጨፍ በተጨማሪ ለገዳዮቹ መሳከሚያ፣ ለሰርግ መደገሻ፣ ለግል መርከብና ለአውሮጵላን መግዣ መዋሉ  ገሃድ ሆነ፡፡ ብዙ ሰሚ አላገኘችም እንጂ ገሃድ ከመውጣቱም በፊት አንድ የሜቴክ ሰራተኛ አጋለጠች፡፡ (ይኸንን ቆርጠውና አጣብቀው ይመልከቱ) https://ethsat.com/2017/08/esat-menalesh-meti-former-employee-metec-exposing-corruption-august-2017/

ከቦንድ መቦንደድ ውድቀት ትምህርት መውሰድ ያቃታቸው ጉዶች ከአምስታ አመታት በፊት ደግሞ ለገሰ በካድሬነት አሳድጎና በጆሮ ጠቢነት አስቀስሶ ሕዝብ ለመፍጀት ለሃያ አመታት እንደ እቃ ሲጠቀምበት ለኖረው ተቅለስላሽ እባብ ፓስተር ፈንድ መፈንደድ ጀመሩ፡፡ እነዚህ ፈንድ ፈንዳጆች ከአባ የሻነው ትልም አነሱ፡፡

አባ የሻነው አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የትል ታሪክ ደጋግመው ይተርኩልን ነበር፡፡ አባ የሻነው "ተትሏ እንማር!" ይላሉ ራሳቸውንም እንደተማሪ በመቁጠር፡፡ "ትሏ ዛፍ ለመውጣት ስትሞክር ወደቀች፤ አንድ በሉ፡፡ እንደገና ሞክረች ግን ነጠረች፤ ሁለት በሉ፡፡ አሁንም እንደገና ስትንጠለጠል ዘች አለች፤ ሶስት ብሉ፡፡ ዘች ታለችበት ተነስታ እንደገና ተንጠለጠለች፤ ግን ተመልሳ እርፉቅ አለች፤ አራት በሉ፡፡ እርፉቅ ታለችበት ተነስታ አሁም ግንዱን በትንሹ ወጣች፤ ግን እንደገና ተንደባለለች፤ አምስት በሉ፡፡ ተተንደባለለችበት ተነስታ ተበፊቱ የበለጠ ርቀት ዛፉን ወጣች፤ ግን ተመልሳ ነጠረች፤ ስድስት በሉ፡፡ ተነጠረችበት ተነስታ ለሰባተኛ ጊዜ ስትሞክር ሰማይ የደረሰውን ዛፍ ምንም እንከን ሳይገጥማት ወጣችው" እያሉ ይተርካሉ ጨረቃ የመሰለ ፈገግታ እያሳዩና ሻሽ የመሰለ ጺማቸውን እያፍተለተሉ፡፡

ከትረካው በኋላም አባታችንና መምህራችን አባ የሻነው "በሰባተኛው ዙር ትሏ ለምን የተሳካላት ይመስላችኋል?" ብለው ሲጠይቁ "በሰባት ስላሴ ስለሚውል፣ ተስፋ ስላልቆረጠች ...ወዘተርፈ" እያልን እንመልሳለን፡፡ እርሳቸውም "እርግጥ ነው ተስፋ ያልቆረጠን ስላሴም ይረዳል!" ብለው የምንሰጠውን መልስ ሳያጣጥሉ "ትሏ የተሰካላት ተእያንዳንዷ ልምድ ትምህርት በመውሰድዋና ያደናቀፏትን መንገዶች ትታ ሌላውን በመከተልዋ ነው" ብለው  ተልምድ የመማርንና የተለያዬ መንገድ የመከተልን ጠቀሜታ ያስተምራሉ፡፡

የአባ የሻነው ትል ያህል ተልምድ መማር ተስኗቸው ስለ ቦንድ እጃቸው ውሀ እስቲቋጥር የጣፉት፣ ላንቃቸው እስቲደርቅ የሰበኩት፣ ልሳናቸው ጥረቅም እስቲል የዘፈኑትና መቀመጫችርውን እስቲያልባቸው ያረጠረጡት ህሊናቸው የሸጡ አለዚያም የተንዘላዘሉ የለገሰ ቦንድ ካድሬዎች ነበሩ፡፡ አለዚያማ ሰይጣንና ለገሰን እንኳንስ ቆመው ሞተውስ ከዘልዛላ በቀር ማን ያምናቸዋል?

የሚያዝ የሚጨበጥ ጭራ የሌለው ለገሰ፤ የሰፈሩን ባንክ በመዝረፍ ባደባባይ ውንብድናውን የጀመረው ለገሰ፤ በአስር ሺ የሚቆጠሩ የመንደሩን ጎረምሶችና ኮረዳዎች እንደ ሳር አሳጪዶ አገራችንን የባህር መተንፈሻ የነሳት ለገሰ፣ በርሃብ የረገፈውን ሕዝብ ስንዴ እየሰረቀ ኬሻውን ባሸዋ የሞላው ለገሰ፤ ለፖለቲካ ፍጆታ የቅዬውን ሕዝብ በቦንብ ያስጨረገደው ለገሰ፣ አማራን ለማዳከምና ለማጥፋት ድንጋዩን ብቻ ሳይሆን ጠጠሩን፣ አሸዋውንና አፈሩን የፈነቀለው ለገሰ፣ በአያቶቻችን ደምና አጥንት የከበረውን መሬታችንን ለሥጋና ለነፍስ አባቱ ሱዳን የሰጠው ለገሰ፣ ሕዝብን በቋንቋ ጎራዴ ያቃላው ለገሰ፤ ስንቱን ባልታወቀ ወህኒ ያሰቃየው ለገሰ፣ ስንቱን እያሰደደ ባባህር ያስበላውና በጭራቆች ያሳረደው ለገሰ "ቦንድ" ብሎ ሲጮህ ቦንደኞቹም ተከትለው እንደ ገደል ማሚቶ "ቦኦ...ንድ...ቦኦ..ንድ" እያሉ አስተጋቡ፡፡ ሳጥናኤል የእግዚአብሔርን ቃል እየተናገረ እንደሚያታልለውም ለገሰ "ራዕይ፣ ታድሶ... ህዳሴ" እያለ ጫቱን እየቃመ ሲጀነጅን ቦንደኞቹም ተከትለው "አዎ ልማት፣ ታድሶ፤ ህዳሴ! ያገር ጉዳይ! የሕዝብ ጉዳይ!" እያሉ ተሽኮረመሙ፡፡

መሽኮርመሙ ከሞቀ ውሀ እንደ ገባ ጨው ፍርክስክስ አርጓቸው ነፈሰ-ገዳዩንና ከሀዲውን ለገሰን እንቃወማለን እሚሉት ሁሉ የቦንድ ካድሬ ሆነው ቁጭ አሉ፡፡ ሌላው ቀርቶ ሕዝብ እንደ ጫካ ሲጨፈጨፍ ድምፃቸው ተሰምቶ እማይታወቅ ተሽኮርማሚ ዲዳዎች በጥሑፍና በራዲዮ ቦንድ፤ ታሐድሶ፤ ህዳሴ በሚሉት ቃላት አፋቸውን ፈቱ፡፡ ስንቶቹ ከንቱ ፕሮፌሰሮችና ዶክተሮች ከስማቸው ዳር ፒኤች ዲ፣ ኤም ዲ ወዘተርፈ  እሚሉ ማእረጎች እያስቀመጡ ድጓ እሚያካክል ዝባዝንኪ እየጣፉ አንባቢን አባተሉ፡፡ ስንቶች አቀንቃኞች "ህዳሴ፣ ራዕይ፣ ታድሶ፣ ልማት" እያሉ መስክ ግጦ እንደ ጠገበ አለሌ አክላሉ፡፡ ስንቶቹ ዘፋኞች ሙሴ የተሻገረውን ባህር የሸጠውን ለገሰን "ባህር አሻጋሪው ሙሴ!" እያሉ በሌለ ባህር አፋቸውን እንደ ሰማይ ከፍተው ተሕዝብ፣ ተእግዚአብሔር፣ ተህሊና፣ ተእውነትና ተታሪክም እስከ መጨረሳው ተቀያየሙ፡፡ ስንቶች ከርሳሞች የለገሰን ቦንድ ለመግዛት እንደ ቡችላ ጅራታቸውን ወትፈው ተንጦሎጠሉ፡፡

ከአምስታ ዓመታት በፊት ደግሞ በኸርማን ኮን ወንበር የወጣው አባትዮው ለገሰ ሞቶ እባቡና ፓስተሩ ልጁ በኸርማን ኮን ወንበር ሲወጣ ለለገሰ የተዘፈነው ዘፈን ተደገመ፡፡ ባህር አሻጋሪው ሙሴ ተዘፈነ፡፡ "ምሁራን"፣ ካድሬዎች፣ ዘፋኞች፣ የፖለቲካ ተንታኞችና እነዚህን የሚከተሉ መንጋዎች በመዝሙር፣ በዘፈን፣ በፌስ ቡክ፣ በትዊተር፣ በሬዲዮና በቴሌቪዥን ፕሮግራሞች፣ ድጓ በሚያካክሉ ጽሑፎች ልሳናቸው እስቲዘጋና ኮቢያቸው እስቲደርቅ እባቡን ፓስተር አወደሱ፡፡ ፓስተሩ በካድሬነት፣ በጆሮ ጠቢነት፣ በኮሎኔልነት፣ በአስተዳዳሪነት፣ ከአባቱ ከለገሰ ጋር በገደላቸውና ባሰቃያቸው ዜጎች ጦር ሰደዱ፡፡ አንዳንዶች እንዲያውም ከእግሩ ሥር እንደ አሽከር ተወሸቁ፤ ሌሎችም በፍቅር አብደው ከተኸሻውና ከደረቱ ወደቁ፡፡ አያሌ "ምሁራን" ለኮር አባሉ የኢህአዴግ ሊቀመንበር የሃያ አራት ሰዓት ካድሬ ሆኑና አረፉ፡፡ ካድሬነታቸው እየበረታ ሲሄድም ከመዝሙሩ፣ ከዘፈኑ፣ ከስግደቱ፣ በፍቅር ሙዝዝ ከማለቱም አልፈው ፈንድ ከፈቱና ቂሉን ሕዝብ ማለብ ጀመሩ፡፡

ፈንድ የተሰበሰበልት ፓስተር ግን ከአባቱ ለገሰ አገዛዝም የበለጥ የአማራን ዘር ፍጅት በመላ አገሪቱ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ እንደ ሰደድ እሳት አቀጣጠለው፡፡ የፓስተሩ አገዛዝ የትግሬ ነጣ አውጪ የተነጠቀውን ስልጣን ለማስመለስ ሲፍጨረጨር የአማራ ሰራዊትና ፋኖ መከታ ሆኖ አዳነው፡፡ ይህ አገዛዝ የተሰውለትን የአማራ ሰረዊትና ፋኖዎች እንደ ልማዱ ክዶና ትጥቅ አስፈትቶ እርስት አልባ የማድረጉና የዘር ፍጅቱን ከዳር ለማድረስ የሰላም ቁማሩን እየዘፈነ ነው፡፡ ትናንት በኢትዮጵያን የዘፈን ቁማር  አማራን ያዘናጋው ዛሬም ያለምንም ሐፍረት በሰላም የቁማር ዘፈን ቀፍድዶ እርስት አልባ ሊያደርገውና ሊያጠፋው ቁማሩን እያጧጧፈ ነው፡፡

አሁንም በእንደዚህ ዓይነት የጭራቅ ቁማሮች የሚዘናጋ አማራ ካለ የእንግዲህ ልጅ ነው፡፡ ለሰላሳ ሶስት ዓመታት አማራን ሲጨፈጭፉ፣ አገር አልባ ሲያደርጉ፣ ሊጥና ጭልፋ ሳይቀር ሲዘርፉ  የኖሩ ጭራቆችን አሁንም የሚያምን ታለ እግዚአብሔር እንዲያስተውልና ተልምዱ እንዲማር አይምሮ ሰጥቶ በአምሳሉ ያልፈጠረው ተሰው በታች የሆን ፍጡር ነው፡፡ ተአማራ ደጅ አፍጦ የመጣው ሰላም ሳይሆን አገር አልባ ላለመሆንና ላለመጥፋት የሚደረግ  የረጅም ጊዜ የህልውና ትግል ነው፡፡ አንዱ እርስት ቀሚ ሌላው ተቀሚ፣ አንዱ ገዳይ ሌላው ተገዳይ፣ አንዱ አሳሪ ሌላው ታሳሪ፣ አንዱ አሳዳጅ ሌላው ተሰዳጅ ሆኖ የሰላም ቁማርን መዝፈን በሰው ህሊና ብቻ ሳይሆን በመለኮትም መቀለድ ነው፡፡ አመሰግናለሁ፡፡

https://amharic-zehabesha.com/archives/126545

ዓባይን ማን መቼ ይገድበው? http://www.zehabesha.com/amharic/wp-content/uploads/2014/06/Abay.pdf

🏗ጋዜጠኛ መታሰቢያ ቀጸላ (ምን አለሽ መቲ) እና ወ/ሮ ቤተልሄም ግርማ የቀድሞ የሜቴክ ሰራተኛ ድርጅቱ ውስጥ ስለሚካሄደው ሙስና አጋለጡ።https://ethsat.com/2017/08/esat-menalesh-meti-former-employee-metec-exposing-corruption-august-2017/

መጀመርያ የካቲት ሁለት አስራ አንድ ዓ.ም. እንደገና ሚያዚያ ሁለት ሺ አስራ አምስት ዓ.ም.
https://amharic-zehabesha.com/archives/181998

No comments:

Post a Comment

https://youtu.be/VUfa5eupQTc?si=Zm73w18dFB27xlqD       https://youtu.be/LcFmz2Xq5MY?si=7uP6VZsd2ksEulUf   https://youtu.be/7dUVmj8go7s?si=Px...