Thursday, March 30, 2023

የውጭ እርዳታና ድጎማ ለቀን ጂቦች አመች ሁኔታ ይፈጥራል - አክሎግ ቢራራ (ዶር)
የውጭ እርዳታና ድጎማ ለቀን ጂቦች አመች ሁኔታ ይፈጥራል

አክሎግ ቢራራ (ዶር)

ኢትዮጵያና የእርዳታ ታሪኳ

ብዙዎቻችን ሰፋ ያለ ትንታኔ ለማንበብ ፈቃደኛ አይደለንም። ወደ ኋላ ዞር ብሎ ማየት ግን የአሁኑንና የወደፊቱን ሁኔታ ለመቃኘት ይረዳናል። የዚህ ወቅታዊ ትንተና ዋና ምክንያት ኢትዮጵያን ከድህነት አሮንቃ ለማውጣት የሚቻለው አገርንና መላውን ሕዝቧን በማፍቀርና በማሰቢ ባለቤትና ኢላማ አድርጎ የሚሰራ የመንግሥት አመራር ከሌለ የውጭ ድጎማና እርዳታ የጅቦችን ኪሶች ይሞላል፤ ጡንቻ ይሰጣል እንጂ ተራውን ሕዝብ ሊረዳ አይችልም የሚል ነው።

የውጭ ድጎማ፤ ብድር ታሪክና ሂደት

ኢትዮጵያ የጣልያንን ፋሽስት ኃይል እንደገና አሸንፋ ነጻነቷን ከተጎናጸፈች በኋላ በሁለተኛው የዓለም ጦርነት አጋር የነበረችው ዩናይትድ ኪንግደም ለኢትዮጵያ እርዳታ መስጠት ጀመረች። እንግሊዝ እርዳታዋን በ 1952 አቋረጠች፤ አሜሪካ ተካቻት። ከ 1950-1970 ባለው ጊዜ መካከል ኢትዮጵያ ከአሜሪካ፤ ከዓለም ባንክና ከሌሎች ለጋሶች ያገኘችው የእርዳታ መጠን $600 ሚሊየን ይገመታል። አንድ ሶስተኛ የሚሆነውን የለገሱት አሜሪካኖች ናቸው። የሶቭየት ህብረት $100 ሚሊየን፤ ዓለም ባንክ $121 ሚሊየን ለግሰዋል። የእርዳታው መጠን በዓመት ሶስት ሚሊየን ዶላር ይገመታል። በአሁኑ ወቅት፤ አሜሪካ ብቻ በያመቱ ለኢትዮጵያ የምትለግሰው አንድ ቢሊየን ዶላር ነው። አሜሪካ ለደርግ በጠቅላላ በአስራ ሰባት ዓመታት የለገሰችው ዛሬ በአንድ ዓመት ለብልጽግና መንግሥት ከምትለግሰው አይበልጥም ነበር ማለት ነው።

ዓለም ባንክ የግል የብድር አገልግሎት ለኢትዮጵያ የምታቀርበው በ International Finance Corporation (IFC) አማካይነት ሲሆን ኢትዮጵያ የዚህ ድርጅት አባል የሆነችው በ 1956 ነው። ለኢትዮጵያ በዝቅተኛ ወለድ እስከ አርባ ዓመት ድረስ የሚከፈል ብድር ወይንም የማይከፈል ድጎማ የሚሰጠው የ International Development Association (IDA)  ነው። ኢትዮጵያ አባል የሆነችው በ1961 ነው። ኢትዮጵያ በሁለቱም መንገዶች እርዳታ የምታገኝበት መንገድ አለ። በተጨማሪ፤ ሁኔታዎች አመችና ትርፋማ እስለሆኑ ድረስ የግል አትራሪ ድርጅቶች የካፒታል ፈሰስ ያደርጋሉ። በዚህ በኩል ከፍተኛውን ደረጃ የያዘችው ቻይና ናት።

እርዳታ ለምን አስፈላጊ ሆነ?

ኢትዮጵያ የካፒታል፤ የእውቀት፤ የቴክኖሎጅና ተዛማጅ ድህነት ስላለባት ነው። እርዳታ ሲባል በገንዘብ ብቻ የሚሰጠው አይደለም። ስዊድን የንጉሱን ክቡር ዘበኛ አሰልጥናለች። ህንድ ለኢትዮጵያዊያን የከፍተኛ ትምህርት አገልግሎትና ድጋፍ ሰጥታለች፤ አስተማሪዎች ወደ ኢትዮጵያ ልካለች። በአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት አንዱ አስተማሪየ ህንድ ነበር። በሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት አብዛኛዎቹ አስተማሪዎቸ “የሰላም ልኡካን” ተብለው የሚጠሩ አሜሪካኖች ነበሩ። አሜሪካ ብዙዎቹን የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ደግፋለች፤ የትምህርት እድል ሰጥታለች። ተቋማትን መስርታለች።

በደርግ መንግሥት የኢትዮጵያ የውጭ ግንኙነት ተለውጦ፤ አገሪቱ አብዛኛውን ድጋፍ ታገኝ የነበረው ከሶቭየት ህብረት አገሮች ነበር፤ ከምስራቅ ጀርመን፤ ከቸኮስሎቫክያ፤ ከራሽያና ከሌሎች፤ የመንንና የኩባን ወታደራዊ ድጋፍ ጨምሮ። እርዳታው መሳሪያና ስልጠናን ያካተተ ስለሆነ በገንዘብ አልተተመነም። ግን ግዙፍ ነው። ብዙ ሽህ ኢትዮጵያዊያን በሶቭየት ህብረት የትምህርት እድል አግኝተዋል። የሶቭየት ህብረት አገሮች አብዛኛዎቹን የደርግ ካድሬዎች አሰልጥነዋል። በልዩ ልዩ የሳይንስና የቴክኖሎጅ ትምህርት ለተሳተፉ ኢትዮጵያዊያን እድል ሰጥተዋል። የዚህን ጥቅም ፋይዳነት መርሳት የለብንም። በገንዘብ ቢተመን ኖሮ ግዙፍ ነው። በቀውጢ ቀን ለኢትዮጵያ ድጋፍ የሰጡትን ወዳጆቻችን ባንረሳቸው መልካም ነው።

ትምህርትና እውቀት የስልጣኔ መሰረት ስለሆነ፤ በዚህ ዘርፍ ለኢትዮጵያዊያን እርዳታ የሰጡ አገሮች ሁሉ የገንዘብ ድጎማና ብድር ከሰጡት የበለጠ ሊመሰገኑ ይገባቸዋል። ምክንያቱም፤ ትምህርትና እውቀት አይሰረቅም፤ አይነጠቅም። አንድ አባባል አለ። “አንድን ሰው አሳ ብትመግበው፤ ለአንድ ቀን ብቻ” ትረዳዋለህ። “ይህን ሰው አሳ እንዴት እነሚያጠምድ ወይንም እንደሚይዝ ብታስተምረው ግን ህይወቱን ሙሉ ትመግበዋለህ”ይባላል።፡ ትምህርት ድህነትን ለመቅረፍ ወሳኝ ነው። ታዳሚው እንዲያጤነው የፈልግሁት፤ በደርግ መንግሥት አሜሪካኖችና ዓለም ባንክ፤ አይ ኤም ኤፍ እርዳታቸውን አቁመው ነበር ። እርዳታው የቀጠለው ለተራቡ ወገኖቻችን የምግብ ድጋፍ በመስጠት ዙሪያ ነው፡፡ ብሊንከን በቅርቡ ወደ ኢትዮጵያ ሂደው ቃል የገቡት $330 ሚሊየን ዶላር እርዳታ ፈሰስ የሚሆነው ለሰብአዊ ድጋፍ መሆኑ አግባብ አለው።  ፍትሃዊ ስርጭት እንደሚካሄድ ተስፋ አደርጋለሁ።

እርዳታና የውጭ ግንኙነት ወይንም የፖለቲካ ጥቅምና አቋም የተያያዙ ናቸው። የደርግ መንግሥት ከወደቀ በኋላ የምእራብ አገሮች ለኢትዮጵያ መንግሥት የሚሰጡት እርዳታ እየጨመረ መሄዱ አያከራክርም። በዚህም መሰረት ህወሓት መራሹ ኢህአዴግ ሥልጣን ከያዘ በኋላ ለኢትዮጵያ የሚሰጠው የእርዳታ መጠን ከፍ እያለ ሄዷል። እዳውም እየጨምረ የሄደበት ዋና ምክንያት ለዚህ ነው።

የአጠቃቀም ክፍተትና ስህተት

ኢትዮጵያ እርዳታውን፤ ድጎማውን፤ ብድሩን ለልማትና የስራ እድል ለመፍጠር ብትጠቀምበት ኖሮ ችግር ወራሽ፤ እዳ ተሸካሚ እና እዳን ለመክፈል ሌላ የውጭ ምንዛሬ ተበዳሪና ለተከታታይ ትውልድ የእዳ ሸክም አሸጋጋሪ አገር ባልሆነችም ነበር። ሌብነቱ፤ ምዝበራው፤ ሙስናው፤ ግዙፍ ኃብት እየተሸሸገ ከአገር መሸሹ ሁኔታውን አባብሶታል።

“ጅቦች” ተብለው የተሰየሙት ህወሃቶች ከሥልጣን ከተወገዱ በኋላ የብልጽግና መንግሥት ተተኪዎች የባሰውን ከጅቦች የላቁ ጅቦች፤ ቀመኞች፤ ሙሰኞችና ዘራፊዎች ሆነዋል።

ይህንን ሃተታ ግልጽ ለማድረግ በአምስት መሰረታዊ ሃሳቦች ዙሪያ እከፍለዋለሁ፤

አንድ፤ ብድርና እዳ አዲስ ነው ወይንስ የቆየና የተወረሰ ክስተት?

ብድር፤ ድጎማና እዳ የቆየና ተከታታይ የሆነ ታሪክ አለው። በዚህ ሃቅ ለመከራከር አይቻልም። ኢትዮጵያ በኦፊሲል ደረጃ እርዳታ መቀበል ከጀመረች 73 ዓመታት ሆኗታል፤ አሁንም ጥገኛ ናት።

ከታች በመረጃ እንደማሳየው፤ ህወሓት መራሹ “ፈጣን እድገት” ለማሳየት የቻለበት ዋና ምክንያት ለጋስ አገሮችና አበዳሪ ድርጅቶች ግዙፍ ድጎማና ብድር ስለሰጡ ነው::

የኢትዮጵያ የንፍስ ወከፍ ሕዝብ ገቢ ዝቅተኛ ስለሆነ፤ ከታክስና ከቀረጥ የሚገኘው ገቢ ከካፒታል ባጀቱ ፍላጎት ጋር ሊመጣጠን ስለማይችል፤ ለእድገቱ ወሳኝ ግብአት የሆነው እርዳታው (Foreign aid) ነው።

ባለፉት አስር ዓመታት ኢትዮጵያ ተከታታይ እድገት ካስመሰከሩ አገሮች መካከል ደረጃዋ ክፍ እንዳለ አያከራክርም። እድገቱ የተካሄደው ግን በድጎማ ነው፤---ለምሳሌ መሰረተ ልማት፤ ግድቦች፤ ትምህርት ቤቶች፤ የኢንዱስትሪ ፓርኮች፤ ስታዲየሞች፤ የሃዲድ ስራዎች፤ ህንጻዎች፤ መሰብሰቢያ አዳራሾች ወዘተ።

የእድገቱ ሞተር ማነው?

የግሉ ክፍል ሳይሆን፤ የፓርቲ፤ የፌደራልና የክልል መንግሥታት፤ ከገዢው ፓርቲ ጋር የተቆራኙ ኩባንያዎችና የግል ተቋማት የውጭ ምንዛሬውን ይሻሙት እንደ ነበረ መረጃዎች ያሳያሉ። ይህ ሁኔታ ሌብነቱን፤ ድጎማውን፤ ሙስናውን አባብሶታል። የመንግሥት ሚና ዳቦ ማምረት ሊሆን አይችልም። ሚናው የተቀነባበረ የልማት እቅድ አውጥቶ ሁኔታዎችን ማመቻቸት ነው።

አንድ፤ የክፍተቱ ገጽታ ምን ይመስላል?

 

የረባና ሃላፊነት፤ ተጠያቂነት የሚያሳይ ተቆጣጣሪ ድርጅት ወይንም ተቋም የለም።

የመንግሥቱ ስርዓት እጂግ በጣም ኢ-ፍትሃዊ፤ በሙስና የተበከለና የሚያመክን ነው።

እጂግ በሚዘገንን ደረጃና በተከታታይ የውጭ ምንዛሬው ይሰረቃል፤ ይባክናል፤ ከአገርና ከሕዝብ ይሸሻል።

የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ መዋቅር አልተቀየረም፤ ኢንዱስትሪ አልተሳፋፋም፤ የገጠሩ ኢኮኖሚ ዘመናዊ አልሆነም።

ፍላጎትና አቅርቦት ሊመጣጠኑ አልቻሉም።

የገበያ ቀውስ በግልጽ ይታያል።

የኑሮ ውድነትና የዋጋ ግሺፈት ሕዝቡን አስመርሮታል።

ከሃያ እስከ ሃያ ሁለት ሚሊየን የሚገመት ሕዝብ ጦም አዳሪ ሆኗል።

በቦረና፤ በሶማሌ ክልልና በሃመር ዞን ብዙ ሚሊየን ሕዝብ በድርቅ ምክንያት እየተሰቃየ ነው።

ወጣቱ ትውልድ የስራ እድል የለውም።

ኢትዮጵያ በያመቱ ለሁለት ሚሊየን ዜጎቿ ስራ ለመፍጠር ስላልቻለች፤ ግማሽ ሚሊየን የሚገመት ወጣት፤ በተለይ ሴቶች የቀን ሰራተኛ ሆነው እንዲሰሩ እያመቻቸች ወደ ሳውዲ አረቢያና ሌሎች የአረብ አገሮች ለመላክ ተስማምታለች።

አምስት ሚሊየን የሚገመት የአዲስ አበባ ሕዝብ የውሃ ችግር እያለበት፤ ሸገርና ጫካ በሚባሉ ግዙፍ ፕሮጀክቶች ላይ ግዙፍ የመዋእለንዋይ ፈሰስ ታደርጋለች።

የኢትዮጵያ የእዳ መጠን $30 ቢሊየን ዶላር በላይ ደርሷል። አበዳሪዎች ተጨማሪ ብድር ላይለግሱ ይችላሉ።

 

ሁለት፤ ብድር ለምን አስፈለገ?

 

የኢትዮጵያ ባለሥልጣናት ብድርና ድጎማ ለምን አስፈላጊ እንደ ሆነና ማንኛውም አገር በብድርና በድጎማ ራሱን የቻለ ኢኮኖሚ ለመገንባት እንደማይችል የሚያውቁ ወይንም የሚረዱ አይመስለኝም። እርግጥ ነው ለተወሰኑ ዓመታት፤

ማንኛውም ድሃና ኋላ ቀር አገር ብድር ያስፈልገዋል።

ኢንዱስትሪውን ለመስራትና ለማስፋፋት መሳሪያ ክውጭ መሸመት አለበት።

የገጠሩን ኢኮኖሚ ዘመናዊ ለማድረግ መሰረተ ልማት መስፋፋት አለበት።

የተገዛው መሳሪያ ለምርት ካልዋለ ግን፤ የሚከብረው ኮሚሺን የሚያገኘውን አካልና ሻጩ ይሆናል።

ድጎማና ብድር የሚሰጠው ተደጓሚው ወይንም ተበዳሪው አገር ራሱን ችሎ ከብድር ነጻ እንዲወጣ ነው። ደቡብ ኮሪያ ጥሩ ምሳሌ ናት። የአሜሪካ ድጎማ $30 ቢሊየን እንደ ነበረ አንድ የኮርያ ኢኮኖሚስት በመረጃ አርቧል። ይህ መጠን አሜሪካኖች ለህወሃት መንግሥት የለገሱትን ያህል መሆኑ ነው።

ደቡብ ኮሪያና ሌሎች የምስራቅ ኤዢያ አገሮች ለጥቂት አመታት ብቻ፤ በአማካይ ከሰላሳ ዓመታት በታች ባለ ወቅት፤ ድጎማና ብድር አግኝተው የራሳቸውን ኢኮኖሚ ዘመናዊ ለማድረግ ችለዋል። እኛ ምን ሆኖን ነው? የውጭ ምንዛሬው እንዴት ቢባክን ነው? ማን ፈቅዶ ወይንም ችላ ብሎ ነው?

ድጎማንና ብድርን በሃላፊነት የመጠቀም ግዴታው የተጠቃሚው ወይንም የተበዳሪው አገር እንጅ የደጓሚው ወይንም የአበዳሪው አይደለም። የተራው ሕዝብም አይደለም።

ጥናቶች የሚያሳዩት አበዳሪዎች የኢትዮጵያ ብድር “እንዲቀንስ የሚፈልጉ አይመስልም” የሚል ነው። ምክንያቱም፤ የራሳቸው ጥቅም ጥገኝነትን ይጠይቃል፤ ተበዳሪ ከሌለ አበዳሪ አይኖርም።

የምእራብ አገሮች፤ ዓለም ባንክ፤ አይኤም ኤፍ፤ ሳውዲ አረብያ፤ ኩዌይት፤ ቻይናና ሌሎች አበዳሪዎች የራሳቸው የዲፕሎማሲ፤ የራሳቸው መርህና ስትራተጂ፤ የራሳቸው የንግድና የገቢ ፍላጎት አላቸው። በነሱ መፍረድ አይቻልም። ጥቅማቸውን የማስከበር መብት አላቸው። የኢትዮጵያ መንግሥት የአገሪቱንና የሕዝቡን ጥቅም ለማስከበር ካልቻለ ሕዝቡ በቃችሁ የማለት ግዴታ አለበት፤ መብቱ ነው። ስልጣንን ፈቅዶ መልቀቅ ያልተለመደ ባህል ስለሆነ በፈቃደኛነት ስልጣኑን የሚለቅ የመንግሥት ሃላፊ ይኖራል የሚል ተስፋ የለኝም።

እያንዳንዱ ተበዳሪ አገር የራሱ የልማት ፍላጎት እንዲሟላ ከፈለገ ብሄራዊ ግዴታውን መወጣት አለበት።

የኢትዮጵያን ሁሉን አቀፍ የእድገትና የልማት ደረጃ ለመገምገም፤ የተባበሩት መንግሥታት የልማት ድርጅት በያመቱ የሚያካሂደውን ዘገባ (Human Development Index/ HDI) መመልከት ያስፈልጋል። ባለፈው ዓመት ኢትዮጵያ ከ 191 አገሮች መካከል 175ኛ ነበረች፤ እምብዛም ከዓመት ወደ ዓመት እመርትዊ ለውጥ አታሳይም።

የዓለም ባንክ አካል የሆነው International Development Association (IDA) ለድሃና ኋላ ቀር አገሮች  በዝቅተኛ ወለድና በነጻ ድጎማ የሚሰጠውን ስመለከት ይህ ሁሉ ድጋፍ ከተሰጠ እንዴት ኢትዮጵያ ቢያንስ ቢያንስ ራሷን ለመመገብ አትችልም”? የሚለው መሰረታዊ ጥያቄ ያሳስበኛል። ከ 2,000 ወዲህ ብቻ አይዳ ለኢትዮጵያ $26 ቢሊየን ፈሰስ አድርጓል። በኦፊሲል ከፍተኛውን ድጋፍ ለኢትዮጵያ የሚለግሰው አይዳ ነው። አሜሪካኖች አይደሉም። ሆኖም፤ ይህ ግዙፍ የድጋፍ መጠን በብዙ ሚሊየን የሚገመተውን ርሃብተኛ ሊደርስለት አልቻለም። ምን እየሆነ ነው? ብለን የመጠየቅና የመጎትጎት ሃላፊነት አለብን። ሰው እየተራበ ሸገር፤ ሸገር፤ ጫካ፤ ጫካ ወዘተ እያሉ ሲናገሩ እኔ ይገርመኛል። በየትኛው ዓለም ቢኖሩ ነው ይህችን በድጎማና በልመና ድጋፍ የምትኖር አገር የሚበድሏት? እላለሁ።

ሶስት፤ ብድሩና እዳው ምን ፋይዳ አለው?

በአገርና በሕዝብ ፍቅር በሚመራና ላወቀበት መንግሥት ድጎማውና ብድሩ ማህበረሰባዊና ብሄራዊ ጥቅም እንዲኖረው እያንዳንዱ ዶላር ምርትን ለማሳደግ፤ የስራ እድልን ለመፍጠርና የልማት መሰረቱ ስር እንዲሰድ ሊያደርግ ይችላል፤ ደቡብ ኮሪያ እንዳደረገችው ማለቴ ነው። የብድርና የድጎማ መሰረቱ ይኼው ነው። ዘላላማዊ ሊሆን አይችልም። ከሰባ ዓመታት በላይ አይበቃም? የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ “ላም አለኝ በሰማይ” ሆኗል።

 

ባለሞያውች የሚሉት እያንዳንዱ ዶላር እንዳይባክን፤ እንዳይሰረቅ፤ ኢንዱስትሪዎች እንዲያስፋፋና ለልማት እንዲውሉ ከተደረገ የሚያስገኘው ጥቅም ከአራት እስከ አምስት እጅ አያንስም፤ ከባከነ ግን ውጤቱ ዜሮ በዜሮ ነው።  የባሰውን፤ ብድሩ መከፈል ስላለበት፤ እዳው ለተከታታይ ትውልድ ሸክም ይሆናል የሚባለው ለዚህ ነው። ብድሩ ሳይከፈል ቀርቶ እዳው እየጨመረ ከሄደ፤ እዳውን ለመክፈል ሌላ ብድር ያስፈልጋል ማለት ነው። ይህ ሲሆን ችግሩ ይባባሳል።

አብዛኛው የኢትዮጵያ ብድር በልዩ ልዩ ዘዴ “በቀን ጅቦች፤ በሙሰኞች፤ አሁንም እንደ በፊቱ የእኛ ተራ ነው” ባዮች ከተሰረቀ፤ በተለይ፤ ከአገር ከሸሸ ብድርና እዳው ተደማምሮ ጥገኝነትን ያስከትላል።

እዳ በእዳ ሲተካ፤ የእርስ በእርስ ግጭት፤ ጽንፈኝነት፤ አገር ወለድ ሽብርተኛነት፤ የሞራል ውድቀት ያስከትላል፤ የዋጋ ግሽፈት አይቀርም።

የእዳ ሸክም ለኢትዮጵያ የውጭ ጠላቶች ወንፊቶች ይፈጥራል። ወጣቱ ትውልድ በራሱ መንግሥት ላይ የሚኖረው እምነት እየቀነሰ ይሄዳል፤ ተቃውሞ ይባባሳል።

አራት፤ ኢትዮጵያ ምን ታድርግ?

የኢትዮጵያ መንግሥት ካለፈው የማፍያ-አይነት ድርጅታዊ ምዝበራ ታሪክ ለመማር አልቻለም። ሕዝብ እምቢተኛነት ካላሳየ የገማው ስርዓት በባሰ ደረጃ ይገማል። አትራፊዎችና ተጠቃሚዎች ስለሆኑ፤ “የቀን ጅቦች” ማለቱ ብቻ መርህ ሊሆን አይችልም። አዲስና ተተኪ “ጅቦች” የአገሪቱን ባጀት፤ በተለይ የውጭ ምንዛሬውን እንዳያባክኑት ከተፈለገ፤ ኢትዮጵያ ጠንካራ፤ ነጻና ብሄራዊ ተቆጣጣሪ ተቋማት ያስፈልጓታል። የኢኮኖሚ ፍትሃዊነት መብት ከሰብአዊ መብቶች ጋር አብሮ የሚሄድ ጉዳይ ነው። ኢትዮጵያን በብድርና በውጭ ድጎማ ተማምና ህብረተሰቧን ዘመናዊ ለማድረግ አትችልም። የፈለገውን ያህል ብልጽግና አለ ቢባል ሃቁ ይኼው ነው።

የወቅቱን ከህወሃት የተወረሰና በተተኪዎች የተባባሰ የውጭ ምንዛሬ ተግዳሮትን ለመወጣት መበደር አማራጭ ሊሆን አይችልም። በአሁኑ የብልፅግና አመራር የኢኮኖሚውን፤ የፋይናንሱን፤ የባጀቱን፤ የመሬቱን አጠቃቀም የበላይነት የሚቆጣጠረው አካል አዲስ የማፍያ ቡድን ይመስላል ብል አልሳሳትም። ምንም በልቶ የማይጠግብ ማፍያ!! ይህ የማፍያ  ቡድን የሚከተለው መርህ ለኛና በኛ ብቻ የሚል ነው። ለአገርና ለወገን መቆርቆር የሚባል ነገር የለም። ይሉኝታ የሚባል እሴት አያውቅም። ባንክ ይዘርፋል። የውጭ ምንዛሬ ያባክናል። የኛ ወይንም “ኼኛ” መረን ለቋል። ለሕግና በሕግ አይገዛም።

ኢትዮጵያ የራሷን ብሄራዊ ጥቅም ማስቀደም አለባት። ግን ስርአቱ ለዚህ ደንታ ቢስ ነው። ጥገኝነትና ብሄራዊ ጥቅም፤ ጥገኝነትና ሉዐላዊነት አብረው አይሄዱም።

በኔ ግምገማ፤ ኢትዮጵያ እንደ አሁኑ ወቅት ተዋርዳ አታውቅም ብል አልሳሳትም።

 

ማንኛውም ብድርና ድጎማ የአገሪቱን የማምረትና ስራ የመፍጠር አቅም ማጠናከር መስፈርት ማንጸባረቅ አለባቸው። አለያ ተጠቃሚው የኢትዮጵያ ኢኮኖሚና የኢትዮጵያ ሕዝብ ሊሆኑ አይችልም። ተጠቃሚዎች የቀን ጅቦች፤ ታዝዢ ካድሬዎች፤ አታሪዎች ናቸው።

 

የኢትዮጵያ መንግሥት ከዓለም ባንክ፤ ከአፍሪካ ልማት ባንክ እና ከአይ ኤም ኤፍ የተበደረው እዳ ሁሉ እንዲሰረዝላት ድርድር ለማድረግ መሞከሩ አግባብ አለው። ግን መንግሥት የራሱን የጅቦች ቤት አለማጽዳቱን አበዳሪዎችም ያውቁታል።

ጥናቶች የሚያሳዩት፤ ከአፍሪካ አገሮች መካከል ግማሾቹ የውጭ ብድር እዳቸው እየጨመ፤ ከጠቅላላ ገቢያቸው 50 በመቶ አልፏል። የኢትዮጵያ ዛሬ 60 በመቶ ደርሷል፤ ዘላቂነት የለውም፤ ሸክም ነው።

በአይሜፍ ዘገባ መሰረት በ2021፣ የአፍሪካ አገሮች ጠቅላላ የእዳ መጠን ወደ $726 ቢሊየን ከፍ ብሏል፤ በ 2017 $417 ቢሊየን ነበር። የኢትዮጵያ “በዝቅተኛ $30 ቢሊየን፤ በከፍተኛ $53 ቢሊየን ደርሷል” ይባላል። ግልጽነት ስለሌለ በቅጡ አይታወቅም።

ከጥቂት አመታት በፊት የአይኤም ኤፍ የበላይ ሃላፊ አዲስ አበባ ሄደው የኢትዮጵያ እዳ መጠን “አሳሳቢ ደረጃ ላይ ደርሷል” ብለው አስጠንቅቀው ነበር። ግን ሰሚ አላገኙም። ለሸገርና ለጫካ ይዝና ፕሮጀክቶች ፈሰስ የሚያደርገው ማነው? ብለን መጠየቅ አለብን።

ከጠቅላላው የአፍሪካ እዳ መካከል ቻይና $132 ቢሊየን የሚሆነውን የንግድ ብድር ሰጥታለች። እዳው ካልተከፈለ የተበዳሪውን ግዙፍና አትራፊ ኩባንያዎች የመውረስ እድል አላት። ቻይናዎች ሲወስዱ እየመረጡ የሚረከቡት አትራፊዎቹን ነው። • ቻይና ለኢትዮጵያ ያበደረችው መጠን $13 ቢሊየን  ካለፈ ቆይቷል። ቻይና ለኢትዮጵያ የሰረዘችው ብድር አንዳለ ሰምቻለሁ። ምን ያህሉን? የሚለው ግን ግልጽነት የለውም።

የአፍሪካ አገሮች፤ ኢትዮጵያን ጨምሮ ከተበደሩት ግዙፍ ብድር መካከል 35 በመቶ የሚሆነውን ያበደሩት እንደ ዓለም ባንክ ያሉ ተቋማት ናቸው።

ሰላሳ ሁለት በመቶ (32 %) የሚገመተው ብድር የተሰጠው በግል ባለ ኃብቶች፤ ባንኮች፤ የጡሮታ ድርጂቶች ወዘተ ነው:: ይህ በማያሻማ ደረጃ መከፈል አለበት።

የዓለም ባንክ የአገሮችን የእዳ መጠንን ዘገባ አድርጎ የሚያሳየው መረጃ፤ የኢትዮጵያ መንግሥት የእዳ መጠን በ 2010 $7.3 እንደ ነበረና በአሁኑ ወቅት በአራት ወይንም አምስት እጅ ወይንም አራት/አምስት ጊዜ ጨምሮ ከ$30 እስከ $50 ቢሊየን እንደ ደረሰ ይነገራል። ገንዘቡን ማን በላው? ማን ሰረቀው? የት ገባ?፡

ከዚህ ግዙፍ ብድርና የሚከፈል እዳ መካከል፤ የዓለም ባንክ ድርሻ ለተለያዩ 35 የልማት ስራዎች (Projects) $12 ቢሊየን ፈሰስ ተደርጓል። ይህ አይዳን አይጨምርም።

ለኢትዮጵያ ተሰጠ ከተባለው $9 ቢሊየን መካከል $3 ቢሊየን ከዓለም ባንክ፤ $2.8 ከአይ ኤም ኤፍ፤ ሌላው ከሳውዲ አረብያና ከሌሎች አገሮች ነው ተብሎ ተወርቷል። ይህ ተጨማሪ ብድር ካለፈው እዳ ጋር ሲጨማመር የኢትዮጵያን የውጭ እዳ መጠን ያባብሰዋል እንጅ አይቀንሰውም።

ከላይ እንደ ጠቀስኩት፤ ቢያንስ ቢያንስ፤ ኢትዮጵያ ከዓለም ባንክና ከተመሳሳይ ድርጅቶች የተበደረችውን ብድርና እዳ ሙሉ በሙሉ እንዲሰረዝላት ድርድር መጀመር አለባት። ይቻላል፤ ከዚህ በፊት ተደርጓል። አበዳሪዎቹ አቅም አላቸው። ግን በምን ምክንያትና ለማን ጥቅም ብለው መጠየቃቸው አግባብ አለው።

እየተበደሩ ስርቆት ከሆነ እኔም አንድ፤ እዳውን አትሰርዙ ሁለት፤ ተጨማሪ አታበድሩ የሚል ምክር እለግስላቸዋለሁ።

አምስት፤ ብድሩና እዳው ከኢትዮጵያ ልማት አቅድ ጋር እንዴት ይዛመዳል?

የኢትዮጵያ መንግስት የልማት ራእይ እንዲህ የሚል ነው፤

“ዋናው የአገሪቱ ራእይ መሰረታዊ ዓላማ በ 2025 ኢትዮጵያን ወደ ዝቅተኛ የመካከለኛ ገቢ ያላት አገር ማሸጋገር ነው።” ይህም፤ “የህዝቡን ተሳትፎና አቅም በማጠናከር ወይንም በማጎልመስ፤ ዲሞክራሲን፤ መልካም አስተዳደርንና አገዛዝን፤ ማህበረሰባዊ ፍትሃዊነትንን” መቀዳጀትን ኢላማ ያደርጋል። በፍጥነት የበለጸጉና በመበልጸግ ላይ የሚገኙ አገሮች---ደቡብ ኮሪያ፤ ቻይና፤ ቬትናም፤ ታይላንድ ወዘተ ኢኮኖሚዎቻቸውን ያሳደጉት ከዝቅተኛ አምራችነት ወደ ከፍተኛ አምራችነት በመለወጥ ነው። ከእርሻው ክፍል ወደ መፈብረኩ ወይንም ኢንዱስትሪው ክፍል በመሸጋገርና ለዜጎቻቸውና ለውጩ ገበያ የቁሳቁስ ምርቶችን በማምረትና በማቅረብ ነው። ትምህርና የስራ እድል ከዚህ መዋቅራዊ ለውጥ ጋር አብሮ ይሄድና የሰራተኞች ገቢ ከፍ ይላል፤ኑራቸው ይሻሻላል። የገጠሩ ህዝብ የተሻለ የስራና የኑሮ አማራጮች ይኖሩታል። በትንሽ መሬት ብዙ ይመረታል። እሳክሁን የሚታየው የኢትዮጵያ እድገት፤ አብዛኛው በመንግሥትና በተመሳሳይ የግንባታ ስራና በአገልግሎት (ሆቴል፤ ምግብ ቤት)፤ አሁን ደሞ “ሸገር፤ ጫካ” ዙሪያ የተመሰረተ ነው።

 

 

የፋብሪካና የሌላው የኢንዱስትሪ ስራ ገና አልተስፋፋም። መዋቅራዊ ለውጥ የለም የሚባለው ለዚህ ነው። የፋብሪካ ስራዎችን ለማስፋፋትና የሥራ እድል ለመፍጠር እምቅ አቅም ያለው የግሉ ክፍል ገና ጫጩት ነው። አንድ የዓለም ባንክ ጥናት እንደጠቆመው፤ የኢትዮጵያ የግል ክፍል ከሌሎቹ የአፍሪካ አገሮች ጋር እንኳን ሲነጻጸር “ከአገሪቱ ጠቅላላ ገቢ የሚሸፍነው 9 በመቶውን ብቻ ነው።” የሌሎቹ የአፍሪካ አገሮች የሚሸፍነው “20 በመቶውን ነው።” ማን ጫጩት አደረገው? ፓርቲውና መንግሥት።

ብድሩን የሚሻሙት እነዚህ ክፍሎች ናቸው። በተጨማሪ፤ ሌላ የማይካድ ሃቅ አለ። ይኼውም ብሄር-ተኮሩ የፌደራል ስርዓት ለልማት ማንቆ ሆኗል። ሰላምና እርጋታ የለም። የሕግ የበላይነት አይታሰብም። ሰብአዊ መብቶች ተገርስሰዋል።  ሕዝብን ያማከለ የልማት እንቅስቃሴ የለም። ኢንቬስተሩ እንደ ልቡ ለመንቀሳቀስ አይችልም። ኢንቬትመንት ይፈርሳል። አዲስ አበባ ለመግባት የማይችል አማራ ሆነ ሌላ ምንን ተማምኖ ኢንቬስት ያደርጋል። ያለውንም እየተቀማ ነው።

ስድስት፤ የኢኮኖሚውን መዋቅር ለመቀየር ምን ያስፈልጋል?

የሕግ የበላይንት፤ ሰላም፤ እርጋታና የዜጎች ደህንነት እንዲከበር ማድረግ።

የኢትዮጵያ የዘውግ ፌደራል ስርዓት የፈጠረው አድሏዊይና አግላይነት ገጽታ ያለው የልማት ግብዓቶች አስተዳደር፤ ለምሳሌ፤ የፌደራል ባጀት፤ የውጭ እርዳታና ዳጎማ አመዳደብና ስርጭት እንዲስተካከልና በግልጽነት እንዲመራ ማድረግ።

የግሉን ክፍል የኢኮኖሚ ውድድር፤ የመፈብረክና የኢንዱስትሪ ልማት ትኩርት እንዲሰጠው በተግባር ማሳየት።

ጉቦን፤ ሙስናን፤ ሌብነትን፤ ሙስናንና የኃብት ሽሽትን ሙሉ በሙሉ በሕግ መከልከል፤ ወንጀሎኞችን በማያሻማ ደረጃ መቅጣት፤ ሚና እንዳይኖራቸው ማድረግ።

ባለሥልጣናትና ሌሎች ኃላፊዎች ግልጽነትና ሃላፊነት የሚያንጸባርቅ ሞያተኛነት እንዲያሳዩ ማድረግ። ችሎታ የሌላቸውን ሙሰኞችን ከስራቸው ማባረር።

ለወጣቱ ትውልድና ለሴቶች ልዩ ትኩረት ሰጥቶ የስራ እድል መክፈት፤ የግል ተቋም መስርተው ስራ እንዲፈጥሩ አቅማቸውን ማጎልመስ፤ ብድር በዝቅተኛ ወለድና ያለመያዢያ (collateral) እንዲያገኙ ማመቻቸት። ባንኮች ይህን መርህ እንዲተገብሩ መመሪያ መስጠት።

የውጭ ምንዛሬ ምርትን ለማሳደግ፤ መዋቅሩን ለመለወጥ እንዲውል መስፈርቶች ማዋጣትና ስራ ላይ ማዋል።

የቅንጦት እቃዎችን ከውጭ መገብየት ሁኔታውን ስላባባሰው ለተወሰነ ጊዜ ይህን ገበያ ማቆም።

ለውጭ ምንዛሬውና ለእዳው አስቸኳይ መፍትሄ መፈለግ።

ለፖለቲካው አመራር ሁከትና ማነቆ የሆኑትን ተግዳሮቶች በውይይትና በድርድር በአስቸኳይ መፍታት።

ሰባት፤ እዳ ቢሰረዝ ሌላ እዳ እንዳይከሰት ምን ይደረግ?

የሚለው ጥያቄ አግባባ አለው። ለዚህ መልሱ፤ ኢትዮጵያ ትኩረት ማድረግ ያለባት ከኢንቬስትመንትና ከንግድ ላይ ይሁን እላለሁ። ብድር መቆም አለበት። ከጥቅሙ ጉዳቱ እንደሚያመዝን ያለፈው የሰባ ሶስት ዓመታት የብድር ታሪካችን ዋና ምስክር ነው። ዓለም ባንክና አይ ኤም ኤፍ የኢትዮጵያን ብቻ ሳይሆን የመላውን የጥቁር አፍሪካን ችግሮች አባብሰውታል።

ይህን ክፍል ለማጠቃለል፤ እነዚህ ተቋማት ባላቸው ዓለም አቀፍ ተሰሚነትና ተቀባይነት መሰረት ከኢትዮጵያ ሕዝብ ተሰርቆ በውጭ ባንኮችና በሌሎች ተቋማት በልዩ ልዩ ስሞችና መንገዶች የተደበቀው ከአርባ ቢሊየን ዶላር በላይ የሚገመት ኃብት እንዲመለስ ዘመቻ ቢደረግ አስተዋጾ ሊያደርጉ ይችላሉ። ብድር በብድር ከመተካት ይልቅ አንድ፤ የኢትዮጵያ አንጡራ ኃብት እንዲመለስ ቢያደርጉ፤ ሁለት፤ የኢትዮጵያ መንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣናት የውጭ ምንዛሬንና ባጀትን እንዳያባክኑ ማስጠንቀቂያ ቢሰጡ፤ ሶስት፤ ሁሉም የውጭ ለጋስ መንግሥታትና አበዳሪዎች የኢትዮጵያ መንግሥት ከፈተኛ ባለሥልጣናት የቅንጥቶና የምኞት ፕሮጀክቶችን (ሸገር፤ ጫካ ወዘተ) ባሰችኳይ እንዲያቆሙ የተቻላቸውን ቢያደርጉ የኢትዮጵያ ሕዝብ ያመሰግናቸዋል።

ጥሪውን የማቅረብ ዘመቻ መጀመር ያለበት የኢትዮጵያ ሕዝብ፤ ዲያስፖራውን ጨምሮ ነው።

ስምንት፤ የውጭ እርዳታ ምን ማለት ነው?

የውጭ እርዳታ ማለት የውጭ መንግሥታት፤ ዓለም አቀፍና የግል ተቋማት፤ በጎ አድራጊ ድርጅቶችና ግለሰቦች ለተጠቃሚ አገሮች ወይንም የህዝብ አካላት የሚያስተላልፉት የካፒታል፤ ጥሬ እቃ፤ መዋእለንዋይ፤ ገንዘብ፤ የጦር መሳሪያ፤ ምግብ፤ መድሃኒት፤ እውቀት፤ አገልግሎት፤ አስቸኳይ ሰብአዊ ድጋፍ ማለት ነው።

ይህ አጠቃላይ ትርጉም ነው። በዝርዝር ሲታይ ግን ዋና ዋናዎቹ ክፍሎች የሚከተሉት ናቸው፤

አንድ፤ በድጎማ-- ያለምንም ወለድና ክፍያ የሚሰጠው ድጎማ (Grant) የሚባለው ነው፤ ድጎማው የተለያዩ መልኮች አሉት፤ ስልጠናን፤ የአቅም ግንባታን ያካትታል።

ሁለት፤ ዓለም ባንክ ለድሃ አገሮች ለረዢም ጊዜ በዝቅተኛ ወለድ (የማስተዳደሪያ ወጭውን ብቻ የሚሸፍን) Soft loan ተብሎ የሚሰጠው ነው። ይህ ከፍተኛውን ድርሻ ይዟል። ዝርዝሩን ከላይ ይመልከቱ።

የዚህ አይነቱ ድጋፍ የሚሰጠው እንደ ኢትዮጵያ ላሉ ድሃ ለሆኑ አገሮች ነው። ይህ ከንግድ አይነቱ ብድር ይለያል። ሶስት፤ ብድር (Loans) ተብሎ የሚጠራው ነው፤ ለሃተታየ መሰረት የሆነው። ብድሩ በውጭ ምንዛሬ የሚከፈል ከሆነ ጣጣ ነው። ለምስሌ፤ ዓለም ባንክ ወይንም ሌላ አካል ያበደረው ብድር በውጭ ምንዛሬ መከፈል አለበት ካለ የኢትዮጵያን ብር አትሞ ለመክፈል አይቻልም። ኢትዮጵያ እዳውን ለመክፈል የውጭ ምንዛሬ ያስፈልጋታል ማለት ነው።

ዘጠኝ፤ ኢትዮጵያ የውጭ ምንዛሬ ከሌላትስ?

በብድር እዳ የተበከሉ፤ በተለይ እንደ ኢትዮጵያ ያሉ ድሃ አገሮች ታሪክ የሚያስተምረን ወይ አበዳሪዎች “ይቅር” ይላሉ ወይንም ለዚህ ችግር መፍትሄ ያቀርባሉ ተብለው የሚገመቱት ዓለም ባንክና አይ ኤም ኤፍ በጋራ ተመካክረው ችግሩን ለመፍታት ይሞክራሉ።

በዚህም መሰረት፤ ከዚህ በፊት በ 2001 ዓ.ም ኢትዮጵያና ሌሎች በድህነትና በብድር እዳ የተበከሉ አገሮች ዓለም ባንክና አይ ኤም ኤፍ በጋራ በመሰረቱት “ከፍተኛ ብድር ያለባቸው ድሃ አገሮች” በተባለው ፕሮግራም መሰረት ኢትዮጵያ የብድር እዳ ቅነሳ ተደረገላት። ይህ የብድር እዳ ቅነሳ ከሃብታም አገሮችና እንደ ዓለም ባንክ ካሉ ዓለም አቀፍ አበዳሪ ድርጅቶች የተገኘውን የብድር እዳ ጨምሮ ነበር። ይህ ቅነሳ የተዛባውን የኢትዮጵያን የንግድ ሚዛን ለማሻሻልና የአገሪቱን የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ለማረጋጋት እንዲረዳ የታቀደ ነበር። አይ ኤም ኤፍ ትኩረት የሰጠው ለንግድ ሚዛኑ (balance of payments ) ሲሆን ዓለም ባንክ ደግሞ ለልማቱ ነበር። ግን፤ የተሰጠው ድጋፍ መዋቅሩን አልቀየረውም። ህወሃት ከሥልጣን ከወረደ በኋላ ሁኔታው አልተሻሻለም። ጦርነቱ አደጋውን አባብሶታል። የቀን ጅቦች ተወግደው የባሱ የቀን ጅቦች ተተክተዋል።

በ 1999, ፤ የቀድሞው የሶቭየት ህብረት አካል የነበሩ አገሮች፤ በተለይ ሩሲያ፤ ለድሃ አገሮች ካበደሩት መካከል $5 ቢሊየን የተገመተ እዳ ሰርዘዋል፤ግዙፍ እዳ። የኢትዮጵያ የውጭ እዳ መጠን በግማሽ የቀነሰው ለዚህ ነበር። ባንድ በኩል ለጋስ በሌላ በኩል ንፉግ የሆኑት የምእራብ አገር አበዳሪዎች የቀነሱት $2 ቢሊየን ነው። ከዚያ ወዲህ የኢትዮጵያ የውጭ እዳ መጠን በአይነትም፤ በስርጭትም፤ በመጠንም ከመቸውም በላይ ጨምሯል። ሙዲስ (Moody’s) የተባለው የአሜሪካው የእዳ መጠንን ገምጋሚ ድርጅት እንዲህ ብሏል። “የኢትዮጵያ መንግሥት በየአመቱ ለውጭ እዳ የሚከፍለው መጠን $1.4 ቢሊየን (ከጠቅላላ የአገሪቱ ገቢ 1.8%) ሲሆን፤ ይህ መጠን ከ 2017/18 እና ከ 2020/21 ላሉት አመታት ይሆናል። www.moodys.com/research/Moodys-affirms-Ethiopias... ይህ ሁኔታ ተባብሷል።

የኢትዮጵያ የንግዱ ሁኔታ አሳሳቢ ነው የሚሉ ታዛቢዎች ብዙ ናቸው። ኢትዮጵያ ከውጭ የምትሸምተው መጠን ባለፉት አስር ዓመታት በያመቱ በአማካይ 12.5% አድጓል። የወጭው መጠን በ2010 $3.6 ቢሊየን የነበረው በ 2016/2017 ወደ $14 ቢሊየን ጨምሯል። በ 2017/2018 ኢትዮጵያ ወደ ውጭ የላከችው መጠን $2.84 ቢሊየን ሲሆን በተመሳሳዩ ወቅት የሸመተችው ግን $15.28 ቢሊየን ነበር። የኢኮኖሚው መዋቅር ካልተለወጠ ኢትዮጵያ ችግሩን ልትወጣው አትችልም፤ ስንዴም ወደ ውጭ ብትልክ።

ሚዛኑ ተዛብቷል የሚለው ዘገባ የመጣውና አይ ኤም ኤፍና ዓለም ባንክ ተጨማሪ ብድር የሰጡበት መሰረታዊ ምክንያት ይኼው ነው። እነዚህ ሁለት አበዳሪ ድርጅቶች  በጋራም ሆነ በግል “ለብዙ ዓመታት የኢትዮጵያ የፓርቲ፤ የግልና የመንግሥት ድርጅቶች ብድር እየጨመረ ሄዷል፤ መሰረታዊ የፖሊሲና መዋቅራዊ ለውጦች ያስፈልጋሉ። የግሉ ክፍል ማደግ አለበት፤ ግልጽነትና ሃላፊነት ያለው የማክሮኢኮኖሚክ ፖሊሲ ያስፈልጋል” ወዘተ ሲሉ ይደመጣሉ። ሃቅ ነው። በተግባር የታየ ውጤት ግን የለም።

አስር፤ ኢትዮጵያ ምን ያህል እርዳታ አግኝታለች?

የኢትዮጵያ ጉድ ተጽፎና ተነግሮ አያልቅም። የኢትዮጵያ የመገናኛ ሚንስትር የነበረው ጌታቸው ረዳ ለሮይተር ሲናገር ያለው ትዝ ይለኛል። “እኛ በቀኝም በግራም እንዋሽ ነበር” ያለውን ማስታወስ ጠቃሚ ነው። በእድገትና በብድርም መጠን ተዋሽቷል። በዐብይ አህመድ መንግሥት ውሸቱ መረን ለቋል፤ ቀይ መስመር የለም።

ሰላምና እራጋታ አለ፤ ውሸት።

ኢትዮጵያ የምግብ ዋስትና ላይ በመድረስ ላይ ናት፤ ውሸት።

ኢትዮጵያ አትፈርስም፤ እያፈረሱ ውሸት።

ግብፅ ልትወረን ነው፤ ውሸት።

ህወሃት እንደ ዱቄት በኗል፤ ውሸት።

ውሸት እንደ ተራ ነገር በሚነገርባት ኢትዮጵያ ሃቁን ለማግኘት አይቻልም። ህወሓት መራሹ ኢህአዴግ ስልጣን ከያዘበት ጀምሮ በኦፊሴል ደረጃ የተገኘው የእርዳታ መጠን ተጨማምሮ ሲታይ ግዙፍ ድጋፍ ተሰጥቷል። በዝቅተኛ መጠን በ 1991 $1.7 ቢሊየን፤ ከዚያ በኋላ በየዓመቱ በአማካይ ከሁሉም ለጋሶች $3.5 ቢሊየን እስከ 2014፤ በ2015 ምርጫ ክርክር ዝቅ አለ፤ እንደገና በ2016 $ 4 ቢሊየን፤ አሜሪካ ብቻ በዚህ አመት $818 ሚሊየን ለግሳለች። በጠቅላላ ሲደመር የተለገሰው “ወደ $53.6 ቢሊየን” ይገመታል (J. Bonas, Ph.D. Economic Commentary, Special to Addis Standard, July 19, 2016። ከዚያ ወዲህ የሚለገሰውና በብድር የሚገኘው የውጭ ምንዛሬና በአይነት ጨምሯል እንጅ አልቀነሰም። በጠቅላላ በኦፊሴል ደረጃ ኢትዮጵያ ከ $100 ቢሊየን በላይ ድጋፍ አግኝታለች። የኢህአዴግና የብልጽግና መንግሥታት ያገኙት የድጋፍ መጠን የአፄ ኃይለ ሥላሴና የደርግ መንግሥታት ካገኙት ጋር ሊነጻጸር አይችልም። የሰማይና የምድር እርቀ አለው። መገምገም ያለብን ውጤቱን ነው።

ለኢህአዴግና ለብልጽግና የተሰጠው መጠን አንተ እንደምትለው ብዙ ሊሆን አይችልም የሚሉ ተከራካሪዎች እንዳሉ አውቃለሁ። ለማሳሰብ የምፈልገው መረጃ የተለገሰው የውጭ ምንዛሬ መጠን በዝቅተኛ አርባ አምስት ቢሊየን ዶላር እንደነበር ከዚህ በፊት በጻፍኳቸው ትንተናዎችና ዘገባዎች በመረጃ ተደግፊ አቅርቤ ስለነበር ዶር ዮናስ ካቀረበው ዘገባ ጋር ይቀራረባል። በተጨማሪ፤ ቻይና ከ 2000 ወዲህ ለኢትዮጵያ የሰጠችው፤ አብዛኛው የንግድ ብድር (ለሃዲድና ሌላ መሰረተ ልማት) $13 ቢሊየን አልፏል። የተሰረዘም ብድር አለ።

በአጭሩ የውጭ እርዳታ ግዙፍ ሆኖ ይታያል። እንቆቅልሽ የሆነው ጉዳይ ግን፤ ኢትዮጵያን ከድህነት አሮንቃ ነጻ አውጥቶ ራሷን የቻለች አገር ለማድረግ አልተቻለም። ከሃያ ሚሊየን በታች ረሃብተኛ እንዳለ ዓለም ባንክ በቅርቡ ባወጣው ዘገባ አይቻለሁ።

ይህ ግዙፍ የውጭ ድጎማና ብድር ለወጣቱ ትውልድ ብዙ የስራ እድል አልፈጠረም። የግሉ ክፍል አሁንም ጫጩት ነው። የእዳው መጠን እየጨመረ ሄዶ ከአገሪቱ ጠቅላላ ገቢ በ 2018/2021 ወደ 60 በመቶ ደርሷል፤ በ 1997 ሃያ አምስት በመቶ የነበረው። የዐብይ መንግሥት ሁኔታውን አባብሶታል ለማለት እችላለሁ።

ለማጠቃለ፤

እኔን ያስጨነቅኝ ይህ ግዙፍ እርዳታና የብድር ክምር ከምርትና ከስራ እድል ፈጠራ ጋር ሊመጣጠን አለመቻሉ ነው።

ማን ተጠቃሚ ሆነ የሚለውን ጥያቄ በተደጋጋሚ አቀርባለሁ። በመሬት ላይ የሚታየው ሃቅ ሌላ ነው። ከተገኘው ግዙፍ እርዳታ ጋር አይዛመድም። ለምሳሌ፤ ኢትዮጵያ ሰሊጥ አምርታ ለምግብ ዘይት ብቻ በየዓመቱ $600 ሚሊየን ወጭ አድርጋ ትሸምታለች። በእርሻ የምትመካው አገር ለስንዴ በየአመቱ $700 ሚሊየን ወጭ ታደርጋለች። ዛሬ ስንዴ አምርታ የዜጎቿን ፍላጎት ለማሟላት አልቻለችም። ስንዴ ወደ ውጭ ትልካለች። ይህ የድገትና የልማት እንቆቅልሽ ነው።

ግልጽነት የሌለባት አገር ስለሆነች፤ የኢትዮጵያ የውጭ የብድር መጠን በትክክል አይታወቅም። በዝቅተኛ ግምት $30 ቢሊየን ይባላል። አንዳንድ ተመልካቾች ወደ $53 ቢሊየን ይጠጋል ይላሉ። ሃቁ በሁለቱ መካከል ሊሆን ይችላል።

በቅርቡ የተለገሰው $9 ቢሊየን ሲጨመርበት እዳውን ማን ይከፍለዋል?

ይህ የውጭ ምንዛሬ አግባብ ላለው፤ በእቅድ ለተደገፈ፤ ግልጽነትና ሃላፊነት ላለው ለምርትና ለስራ እድል ፈጠራ ቢውል (ለመዋቅራዊ ለውጥ) እያንዳንዱ ዶላር ሊያስገኘው የሚችለው ጥቅም አምስት እጅ ሊሆን ይችላል።

ባለሞያዎች፤ ዓለም ባንክን ጨምሮ ድርብርብ (multiplier effect) ይኖረዋል የሚሉት ለዚህ ነው። ብድርና እርዳታ ኢትዮጵያን ዘመናዊ ቢያደርጋት ኖሮ ዛሬ የመካከለኛ ገቢ ካላቸው አገሮች አንዷ ኢትዮጵያ መሆን ነበረባት።

የውጭ እርዳታ፤ ድጎማና ብድር በኢትዮጵያ ቢሰራ ኖሮ (ማለትም ገንዘቡ ባይባክን፤ ባይሰረቅና ከአገር ባይሸሺ ኖሮ) ለኢትዮጵያ እስካሁን የተሰጠው ብድርና ሌላ ድጎማ የምርት ኃይሉን ጨምሮ፤ የስራ እድልን በብዛት ፈጥሮ የአገሪቱን ኢኮኖሚ ጠቅላላ ገቢ ቢያንስ ቢያንስ እጥፍ ያደርገው ነበር። ኢትዮጵያ በማህበረሰባዊ ልማት መስፈርት ከ 191 አገሮች መካከል 175ኛ ናት። በ 2023 የነፍስ ወከፍ ገቢ ሲገመገም፤ የኢትዮጵያ $873 ነው፤ የኬንያ $1,811.
https://amharic-zehabesha.com/archives/181347

No comments:

Post a Comment

https://youtu.be/VUfa5eupQTc?si=Zm73w18dFB27xlqD       https://youtu.be/LcFmz2Xq5MY?si=7uP6VZsd2ksEulUf   https://youtu.be/7dUVmj8go7s?si=Px...