Tuesday, October 11, 2022

አካፋን አካፋ ብሎ ለመጥራት የመቸገር የፖለቲካ ባህል – ጠገናው ጎሹ
October 8, 2022

ጠገናው ጎሹ

ይህንን ግልፅና ቀጥተኛ አስተያየቴን ለመሰንዘር ምክንያት የሆነኝ በሥርጉት ካሳሁን የቀረበውን ሂሳዊ ፅሁፍና በዚሁ ጽሁፍ ላይ Tesfa በተሰኘ ስም  የተሰጠ  ሂሳዊ ትችት መሆኑን ለመግለፅ እወዳለሁ። የፅሁፉን አቅራቢ ስም ምናልባት ከእኔ ድክመት ካልሆነ በስተቀር ብዙም የማውቀው አይደለም።

በፅሁፉ አቀራረብና ይዘት ላይ ትችት የሚያሰጥ አንዳችም ነገር የለም የሚል ደምሳሳ አስተያየት የለኝም። እንደ አንዳርጋቸው አይነት በአንፃራዊ ግምገማ ከራሳቸው የረጅም ጊዜ የፖለቲካ ሰብእና እና የሞራል ከፍታ ወርደው እጅግ በአስከፊ አኳኋን ቁልቁል በመምዘግዘግ የህወሃትን የበላይነት አስወግዶ ሥርዓቱን ግን እጅግ አስከፊና አስፈሪ በሆነ ሁኔታ ላስቀጠለው ሸፍጠኛና ሴረኛ የኢህአዴግ አንጃ (ኦህዴድ/ብልፅግና) ህሊናቸውን (ውስጠ ነፍሳቸውን) ላስረከቡ ወገኖች  መነገር ያለበት ግዙፍና መሪር እውነት ግልፅና ቀጥተኛ በሆነ ቋንቋ  የቀረበበት የመሆኑን እውነታ ግን ማስተባበል ወይም ማጣጣል አይቻልም የሚል ጠንካራ አስተያየት አለኝ።

በፅሁፉ ላይ  Tesfa  በሚል ስም ሂሳዊ ትችት የሰጡትን  በግል ባላውቃቸውም ከረጅም ጊዜ ጀምሮ በባህላዊ መገናኛ ዘዴዎችና በማህበራዊ ሚዲያ በሚሰጧቸው ቅንነትና አገር ወዳድነት በሚንፀባረቅባቸው ነፃ አስተያየታቸው እንደማውቃቸው ለመግለፅ እወዳለሁ። ከላይ በጠቀስኩት ጽሁፍ ላይ በሰጡት አስተያየት መነሻነት የምሰጠው ሂሳዊ አስተያየት ከፖለቲካ አስተሳሰብና አመለካከት ልዩነት ላይ እንጅ ከግል ባህሪና አስተሳሰብ ጋር ግንኙነት የሌለው ስለመሆኑ ግንዛቤ እንዲወሰድ ለማስገንዘብ እወዳለሁ። ይህ  አይነት የግንዛቤ ማስታወሻ  የሚነሳው ማነኛውም ሰው በመርህ ደረጃና በሌላው  መብትና ህልውና ላይ ሥጋት ወይም አደገኛ አሉታዊ ውጤት የሚያስከትል እስካልሆነ ድረስ  በተረዳውና በሚያምንበት ልክ (መጠንና አይነት) ሃሳቡን ወይም አስተሳሰቡን የመግለፅ መሠረታዊ መብቱ ነው ከሚል ፅዕኑ እምነት ነው።

ለመግቢያዬ ይህን ያህል ካልኩ ወደ ሂሳዊ አስተያየቴ ነጥቦች ልለፍ፦

1) ዘመናትን ላስቆጠረውና አሁንም ተዘፍቀን ለምንገኝበት አጠቃላይ ቀውስና ውድቀት አስተዋፅኦ ያደረጉትን ፣ እያደረጉ ያሉትንና መነሻቸው የግለሰብ ወይም የግለሰቦች የፖለቲካ ሰብእና እና የሞራል ዝቅጠት የሆኑትን ጉዳዮች እንደማናቸውም አይቶ መታለፍ እንዳለባቸው ተራና ጊዜያዊ ጉዳዮች አድርጎ ማቅረብ የእውነተኛ ነፃነትና ፍትህ ፈላጊ የመፍትሄ ፍለጋ መንገድ  አካል  ሊሆን አይችልም።

2) “በየትኛው መሥፈርት ነው አንዳርጋቸው የአማራ ጠላት የሚሆነው? ” የሚለውን ጥያቄ እድሜ ልኬን ታገልኩለት የሚሉትን የመሠረታዊ ነፃነትና የፍትህ ሥርዓት እርግፍ አድርገው በመተው አጥብቀው ይፀየፉት የነበረውን ህወሃት መራሽ የጎሳ አጥንት ስሌት የፖለቲካ ቁማር የተካውንና ታይቶና ተሰምቶ በማይታወቅ ሁኔታ የኢትዮጵያን ህዝብ በአጠቃላይና በተለይ ደግሞ የአማራን ማህበረሰብ የቁም ስቃይና የግፍ ግድያ ሰለባ ላደረጉት ኦህዴዳዊያን/ኦነጋዊያን እና ወራዳና ጨካኝ ብአዴናዊያንና ደህዴናዊያን ህሊናቸውን ለሸጡ  እንደ አንዳርጋቸው አይነት የፖለቲካና የሞራል ኮስማኖች  ለምን የአማራ ጠላቶች ይባላሉ በሚል ጉዳዩን ወደ የተራ (የአረቤነት) ደረጃ ለማውረድ መሞከር መሬት ላይ ላለው ግዙፍናመሪር ሃቅ ፈፅሞ ይመጥንም።

3) አዎ! የአማራ አመራር ተብየው የአማራውም ሆነ የሌሎች ንፁሃን ወገኖች ዋነኛ ጠላቶች መካከል አንዱ ነው። ህወሃትን ተክቶ በህዝብ ላይ የማያቋርጥና እጅግ አስከፊ የመከራና የውርደት ዶፍ እያወረደ ካለውና የቤተ መንግሥቱን ፖለቲካ ከተቆጣጠረው ገዥ ቡድን ጋር እጅግ ፀያፍና አደገኛ በሆነ የፖለቲካ አመንዝራነት የተዘፈቁት እንደ አንዳርጋቸው አይነት ወራዳ ወገኖች አይደሉም እንዴ?  ታዲያ አገርን በማቆየት በተደረገውና ለማቆየትም እየተደረገ ባለው እልህ አስጨራሽ ተጋድሎ የእራሱን ጉልህ ሚና የነበረውንና ያለውን የአማራ ማህበረሰብ ከግፈኞች ጋር ሆኖ መከራውንና ውርደቱን ከማራዘም የከፋ የአማራ ጠላትነት አለ ወይ?

4) አዎ! ዛሬም ንፁሃን ጋዜጠኞችና የሰብአዊ መብቶች መደፍጠጥ ያሳስበናል ያሉና የሚሉ ወገኖች ዘብጥያ እየወረዱ ናቸው። ታዲያ ይህንን አይነት ግፍና መከራ እንደ ዶፍ እያወረዱ ከቀጠሉት ሸፍጠኛ፣ ሴረኛ፣ ፈሪና ጨካኝ ገዥ ቡድኖች ጋር በፖለቲካ አመንዝራነት እየተሻሹ ያሉት እንደ አንዳርጋቸው አይነት ወገኖች ከግማሽ እድሜያቸው በላይ ከቆዩበት የእውነተኛ ነፃነትና ፍትህ ሃዲድ ተንሸራተው እራሳቸውን ቆሻሻ ግባ እና ቆሻሻ ውጣ (Garbage In And Garbage Out) በሚል የፖለቲካ አዙሪት ውስጥ የሚርመጠመጡ  ወገኖች አይደሉም እንዴ?

ተጨማሪ ያንብቡ:  ጥቃትን እንደ ግጭት ማቅረብ የግፉአንን ጩኸት መቀማት ነው - ያሬድ ሃይለማሪያም

5)  አገርና ህዝብ እንኳን ማቆሚያ ሊገኝለት አንፃራዊ የእፎይታ እስትንፋስ የሚያሳጣ የመከራና የውርደት ዶፍ ሰለባ ሆነው እንዲቀጥሉ ካደረጉና በማድረግ ላይ ከሚገኙት ዋነኛ  እኩያን ወገኖች መካከል ህወሃትና ኦነግ (ሸኔ) የመሆናቸው ሃቅ መሬት ላይ ተዘርግቶ የሚነበብ በመሆኑ ፈፅሞ ማብራሪያ የሚሻ ጉዳይ አይደለም። ከአራት ዓመታት ወዲህ ደግሞ በአንድ በኩል የቤተ መንግሥቱን ፖለቲካ በተቆጣጠረው ኦህዴድ/ብልፅግና እና በሌላ በኩል ደግሞ  ለምን  ዙፋኔን ተነጠቅሁ በሚል አካኪ ዘራፍ በሚለው ህወሃትና አምሳያዎቹ ጥምረት ከሥልጣን ሽኩቻ በስተቀር ሌላ ምንም አይነት አሳማኝ ምክንያት የሌለውን የመግደል፣ የማገዳደልና የመገዳደል እጅግ አሰቃቂ የፖለቲካ ምንነትንና ማንነትን ከምር ለሚያስተውል እውነተኛ የነፃነትና ፍትህ ፈላጊ ወገን ህሊናን አያቆስልም እንዴ? ምንም አይነት ይሉኝታ በሌለበት አኳኋን ለምድራዊውም ሆነ ለሰማያዊው የበጎ ህይወታቸው መንገድ ዋስትና የሆነውን አንጡራ ህሊናቸውን (ውስጠ ነፍሳቸውን) ለባለጌና ለጨካኝ ተረኛ ኢህአዴጋዊያን ብልፅግናዊያን አሳልፈው የሰጡ እንደ አንዳርጋቸው አይነት ከንቱዎችን የእራሱም ሆነ የአገሩ የኢትዮጵያ ነፃነትና ክብር ከመከራና ከውርደት መውጣት አለበት የሚል ፅዕኑ ፍላጎት ያለው የአማራ ማህበረሰብ ጠላቶች ለይቶ ማየት አይቻልም በሎ እቅጩን መናገርና መነጋገር ተራና የማይጠቅም ወይም አጉል አቴካራ (እሰጥ አገባ) ለምና እንዴት ይሆናል? ለዚህ ነው ነገረ ሥራችን ሁሉ እየፈጩ ጥሬ አይነት ሆኖብናልና ከግልብ የፖለቲካ ስሜትና ከክስተቶች ትኩሳት ጋር ከመውጣትና ከመውረድ ያለፈ የፖለቲካ ማንነቱን ምንነቱን እየለዩና እያስለዩ የግፍ ግድያና የቁም ሰቆቃ ሰላባ እንዲሆን ካደረጉት እኩያን ገዥቡድኖችና ሌሎች ቡድኖች ለይቶ ለማየት እንዴት ይቻላል?

6)  አዎ! የህወሃት ፖለቲከኞች ለዘመናዊውም ሆነ ለባህላዊው የእርቅና የሰላም ጥረት የሚመች የፖለቲካ ሰብእና እና የሞራል እሴት በእጅጉ እንደሚጎላቸው ለመገንዘብ አስተዋይና ቅን ህሊና እንጅ የተለየ ጥናት ወይም ምርምር አይጠይቅም።

በሌላ በኩል ግን ለሩብ ምዕተ ዓመት የህወሃት እኩይ ዓላማና ግብ ታማኝና ርህራሄ ቢስ አገልጋዮች ሆነው የዘለቁትንና ከአራት ዓመታት በፊት ጀምሮ ደግሞ የሥልጣን የበላይነት ሽኩቻውን ወራዳና አዋራጅ በሆኑ ብአዴን ፣ ደህዴን እና ሌሎች  አጋር ተብየዎች አሽከርነት አሸንፈው አገርን ፈፅሞ ታይቶና ተሰምቶ በማይታወቅ ሁኔታ የንፁሃን ደምና የቁም ሰቆቃ ምድር ያደረጉትንና በማድረግ ላይ የሚገኙትን ኦህዴጋዊያን/ብልፅግናዊያን ለአገር አንድነትና ለህዝብ ደህንነት ሲሉ የሚጋደሉ አድርጎ ከማሰብ የከፋ የፖለቲካ አስተሳሰብ እና የሞራልና የመንፈስ ድቀት (ዝቅጠት) ይኖራል እንዴ? አንዳርጋቸውና መሰሎቹስ የዚህ አይነት እጅግ አስከፊ የፖለቲካ ቁማር ውስጠ አዋቂዎችና አማካሪዎች አይደሉም እንዴ? ታዲያ ከዚህ የከፋ የግፍ ሰለባ የሆነው የአማራ ማህበረሰብ ጠላትነት የትኛውና እንዴት ያለ ነው?

7) ሁለቱ የኢህአዴግ የጎሳ አጥንት ስሌት ፖለቲካ አንጃዎች በሥልጣን ሽኩቻ ምክንያት እንደ በጎና ትልቅ የታሪክ ሂደት በምዕራፍ እየከፋፈሉ ላካሄዱትና እያካሄድት ላሉት እጅግ አስከፊ የወንድማማች/እትማማቾች ጦርነት እና እየተካሄደ ነው ለሚባለው ድርድር ተብየ የመክሸፍ (የመጨንገፍ) ፈተና ህወሃትን ብቻ ተጠያቂ የማድረግ እጅግ የተዛባና የመከራውን ዘመን ለማሳጠር የማይረዳ የፖለቲካ አስተሳሰብ  ለምንና ለማን ነው የሚጠቅመው? ሁለቱም አንጃዎች እኩይ የፖለቲካ አረንቋ ውስጥ በተዘፈቁበትና መከረኛውን ህዝብ በደም እንዲቃባ ባደረጉበት ፣ እያደረጉ ባሉበት ሁኔታ ውስጥ እና ይህንኑ የሚያስቆምና ወደ ትክክለኛው የጋራ መፍትሄ የሚወስድ የፖለቲካ ሃይል ከመፍጠር ይልቅ እጅግ መያዣና መጨበጫ በሌለው የፖለቲካ አዙሪት  ውስጥ እየተርመጠመጥን ባለንበት መሪር እውነታ ውስጥ የህዝብ የነፃነትና የፍትህ ጥያቄ አንደኛው አንጃ ሌላኛውን ከምድረ ገፅ በማጥፋት ይመለሳል የሚል አይነት እጅግ የወረደ የፖለቲካ አስተሳሰብ የሚቀነቀነው እንደ አንዳርጋቸው በመሰሉ ሃፍረተቢስ አድርባዮች አይደለም እንዴ? ይህንን አይነት ዘመን ጠገብ የፖለቲካ ድንቁርና እና የሞራል ዝቅጠት  ቆም ብለን ለማየት ለምንና እንዴት እንደተሳነን አሁንም እራሳችንን ለመመረመርና ተገቢውን የእርምት እርምጃ ነገ ሳይሆን ዛሬውኑ ለመውሰድ ፈቃደኞችና ዝግጁዎች ካልሆን ነየፃነትና ፍትህ ፈላጊነታችን እንዴት ትርጉም ሊኖረው ይችላል? 

ተጨማሪ ያንብቡ:  ብአዴን ሆይ! ነፍስ ይማር!!

8) “አባቶች ፣ እናቶች ፣ ቀሳውስትና የእስልምና እምነት ወንድሞችና እህቶች እያለቀሱ ሲለምኗቸው አሻፈረኝ ብለው አሁን ሰላም ፍለጋ ደቡብ አፍሪካ ድረስ ለመሄድ ማሰብ ርካሽነት ነው” የሚለውና አሁንም የቀድሞውን የኢህአዴግ የበላይ ጠርናፊ ህወሃትን ብቻ የመወንጀል የፖለቲካ አስተሳሰብ ከምንመኘው የእውነተኛ ሰላምና ፍትህ ሥርዓት እውን መሆን ጋር እንዴት ሊጣጣም ይችላል?

እውን ከማልቀስ ያላለፈው የእናቶች ጥሪ ለዘመናት በአስከፊ የፖለቲካ ወለድ ወንጀል እጆቻቸው የተዘፈቁትን ሁለት የአንድ ሥርዓት አንጃዎች (ህወሃትና ብልፅግና) ወደ እውነተኛ (የሥርዓት ለውጥን በሚያስከትል ደረጃ) ለማስጠጋት ይችል ነበር ወይ?

የቤተ መንግሥቱ የኢህአዴግ አንጃ ቡድን የሚግታቸውን የለየለት የሸፍጥ ፖለቲካ ፕሮፓጋንዳ  መልእክት እንደሚያደርስ ፖስተኛ ከማመላለስ ያለፈ ፋይዳ ያልታየበት የአባቶች፣ የቀሳውስትና የእስልምና ተካይ ወገኖች ተማፅኖና ልመና  ለዘመናት  ለመጣንበትና አሁንም በአስከፊ ሁኔታ ተዘፈቅን ለምንገኝበት ግዙፍና መሪር ፈተና ፍቱንና ዘላቂ መፍትሄን አምጦ የመውለድ አቅም እንዴት ሊኖረው ይችላል?

10)  አዎ! “የመደመሩ ሂሳብ ወደ መቀነስ ተለውጦ ይኸው አቦይ ስብሃትን የፈታው የብልፅግና መንግሥት ለአገር  አንድነትና ለወገን እኩልነት የሚፋለሙትን እየሰወረ ነው“ የሚለውን አገላለፅ አጠቃላይ እውነትነት ያለው መሆኑን ለመረዳት አያዳግትም።

ገረፍ ከማድረግ አልፈን ልብ ካልነው ግን ፦

ሀ) “ከመደመር ወደ መቀነስ ተለወጠ” ስንል ከመጀመሪያውም የሸፍጠኛና ሴረኛ ፖለቲከኞችን በተለይም በጎ ሠርቶ በራስ የመተማመን ሳይሆን እጅግ ልክ በሌለው የግል ዝናን ሊያተርፍለት በሚችል መናቸውም የውሸት፣ የማታለል ፣ የሸፍጥና የሴራ ፖለቲካ ሰብእና ክፉኛ የተለከፈውን ጠቅላይ ሚኒስትር ተብየ ድርሰት ወንዝ እንደሚያሻግር ፍልስፍና በመውሰድ የራሳችን የፖለቲካ ኮስማናነት ያሳየንበት መሆኑን

ለ)  ለዚህ አይነት በለየለት ሸፍጥ፣ ሴራና ጨካኝ የፖለቲካ ኦርኬስትሬሽን መሳካት እጅግ ጉልህ ሚና ከተጫወቱት መካከል አንዳርጋቸውና መሰሎቹ  የመሆናቸውን መሪር ሃቅ በግልፅና በቀጥታ የሚገልፁትን ወገኖች ተራ በሆነና  በማይጠቅም የፖለቲካ ጨዋታ እንደተጠመዱ አድርጎ የማየትን በእጅጉ የተንሸዋረረ አመለካከታችንን

ሐ) በራሳቸው በነስብሃት ነጋ እጅግ ፀያፍና አስከፊ በሆነ የጎሳ አጥንት ስሌት ፖለቲካ ቁማር ሥር ለሩብ ምእተ ዓመት በፍፁም ታማኝነት ሲያገለግሉ የነበሩና የሥልጣን ሽኩቻውን አሸንፈው የቤተ መንግሥቱን ፖለቲካ የበላይነት በመቆጣጠር አገርን ወደ ምድረ ሲኦልነት የለወጡት ወንጀለኛ የኢህአዴግ አንጃ ቡድኖችን እነ ስብሃት ነጋ ከፈፀሙት ወንጀል ነፃ ሆነው የፍትህና የርትዕ ጠበቃዎች እንደሆኑ አይነት አድርጎ የማሳየትን እጅግ የወረደ የፖለቲካ አስተሳሰባችን ነው የሚነግረን።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ኢትዮጵያ በርግጥ ዴሞክራሲ ይገባታል ወይ?

11) ጀኔራል ፃድቃን ባካሄደው ቃለ መጠይቅ ውስጥ ከቆመበትና ከቆመለት ዓላማ አንፃር የፈለገውን አይነትና ይዘት ያለውን ትርክቱንና የአቋም መገለጫውን መናገሩን እንደ አዲስ ነገር ለማመሳከሪያነት የተጠቀምነውን ያህል የአንዳርጋቸውንና የመሰሎቹን የህዝብን የነፃነትና የፍትህ ትግል ከድተው እነ ፃድቃን አስወልደው ካሳደጓቸውና ያንኑ ሥርዓት እጅግ አስስከፊ በሆነ የተረኝነት የፖለቲካ ሥልጣን በመጠርነፍ አገርን ምድረ ሲኦል እያደረጉ ካሉት ጋር ርካሽ የፖለቲካ አመንዝራነት የሚፈፅሙትን እንደ አንዳርጋቸው አይነት ወገኖች ማሄስ ተራ ወይም ፋይዳ የሌለው ነው የሚሉት የፖለቲካ ትርክት ምን የሚሉት የነፃነትና የፍትህ ፍለጋ አስተሳሰብ ነው?

12) ምናባዊና ንደፈ ሃሳባዊ ከሆነው ዓለም አልፈን የገሃዱን ዓለም የፖለቲካ እና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ልብ ካልነው በየአንዳንዱ አገር የውስጥ ሁለገብ አቅምና ችሎታ ላይ የተመሠረተ ነው ። በዚህ የገሃዱ ዓለም እውነታ ውስጥ እንኳንስ ሞራልና ሥነ ምግባር የዓለም አቀፍ ህጎችና ልማዳዊ አሠራሮች (International Laws And Norms) ወደ መሬት ወርደው የሚፈለገውን በጎ ውጤት የመፍጠር እድላቸው በእጅጉ በፈተና የተሞላ ነው። ይህ ደግሞ የዓለም ፖለቲካና ዓለም አቀፍ ግንኙነት እውቀት ወይም ግንዛቤ ሀሁ ነው።

ይህንን እጅግ ቀላል በሚመስል ግን መሪር እውነትነት ባለው ምሳሌ ማሳየት ይቻላል። አንድ ይበላው ያጣን የምስኪን ድሃ ልጅ ኬክ የመሰለ ዳቦውን በመተከዣነት እየገመጠ መንገድ ላይ የሚዝናና የሃብታም ልጅ ቢያገኘውና እግሩን ተጎንብሶ ከሳመ ከጥጋብ ያተረፈውን ዳቦ እንደሚሰጠው ቃል ቢገባለት ፈፅሞ አያደርገውም ብሎ መከራከር በራበው ሰው (ያውም በህፃን) መፍረድ ነው የሚሆነው ። የህዝብን ርሃብ፣ ጥማትና ደህንነት ግምት ውስጥ በማስገባት ለሃያላን ተፅዕኖ (አላስፈላጊም ቢሆን) የማይንበረከኩ ገዥዎች ፈፅሞ አይኖሩም ለማለት ባይቻልም አብዛኛዎቹ ከእራሳቸው ልክ የሌለው ሥልጣናቸውና ከእርሱ የሚገኘው የግልና የቡድን ጥቅም ሥጋት ላይ የወደቀ መሆኑን ሲረዱ ብቻ ነው ለውጭ ተፅእኖ ፈጣሪ ሃይሎች የሚንበረከኩት።

ይህንን የሚያደርጉት ግን “የእኛ ዘመን ጠገብ መሪር ሃዘንና የደም እንባ ሳይገዳችሁ የውጭ ሃይላትን ተፅዕኖ በመቀበል ያንኑ ክፉ ሥርዓታችሁን ለማስቀጠል ወሰናችሁ?” የሚልን የህዝብ ጥያቄና እሮሮ በሚያመክን ወይም ቢያንስ በሚያለዝብ  የፖለቲካ ጨዋታ ነው። ይህንን ስል በውጭ ሃይሎች ተፅኖም ቢሆን ጦርነት መቆም የለበትም እያልኩ ሳይሆን መሠረታዊ በሆነና ቀጣይነት (ዘላቂነት) ባለው የዴሞክራሲያዊ ለውጥ የእነዚህን እኩያን የፖለቲካ ሃይሎች የመከራና የውርደት ሥርዓት ለመስወገድ እስካልቻልን ድረስ ማቆሚያ የሌለው የፖለቲካ ሥልጣን ሽኩቻቸው እያገረሸ በሚያስከትለው የእርስ በርስ ጦርነት (እልቂት) ሰለባዎች ሆነን እንቀጥላለን ነው።

የትኛውም የውጭ ግንኙነት ጥንካሬና ድክመት በወሳኝነት የሚለካውና የሚወሰነው በውስጣዊው ሁለንተናዊ ጥንካሬና ዝግጁነት እንጅ በተቃራኒው አይደለምና የገንዛ ራሳችንን ቤት ለሸፍጠኛ ሴረኛ ገዥ ቡድኖች የእኩይ ፖለቲካ  መጫወቻነት አሳልፈን እየሰጠን ከእንዲህ አይነት ክፉ ገዥ ቡድኖች ጋር ርካሽና አደገኛ የፖለቲካ አመንዝራነት የተዘፈቁ እንደ አንዳርጋቸውና መሰል ወገኖች ተግባርና ስም በተነሳ ቁጥር አሜሪካኖች ፣ የአውሮፓ ህብረት ሃይላት ፣ ወዘተ ጣልቃ ገቡብን እያሉ ማላዘን ጨርሶ ስሜት አይሰጥም።

13) ” ከሁሉም ጋር ትግልና ከሁሉም ጋር ፉክክር ለማንም አይጠቅምም” የሚለው ማስጠንቀቂያ አይነት መከራከሪያ ግልፅና ግልፅ ከሆነው ከአንዳርጋቸውና መሰሎቹ  የፖለቲካ ዝቅጠትና የሞራል ጉስቁልና ጋር በምንና እንዴት እንደሚገናኝ ለማሳመን አይቻልምና በስሜት ከሚነጉድና የማይገናኘውን እያገናኙ የመከራውንና የውርደቱን እድሜ ማራዘም የለብንም ። እናም  ልብ ያለው ልብ ይበል !!!

 
https://amharic-zehabesha.com/archives/177370

No comments:

Post a Comment

https://youtu.be/VUfa5eupQTc?si=Zm73w18dFB27xlqD       https://youtu.be/LcFmz2Xq5MY?si=7uP6VZsd2ksEulUf   https://youtu.be/7dUVmj8go7s?si=Px...