Wednesday, February 28, 2024

ከመቅዳላ የተዘረፈውና ለጨረታ የቀረበው ቅርሳችን…!! ለጨረታው ቀረበው የመቅደላ ቅርሳችን ወደ ሀገሩ፣ ኢትዮጵያ እንዲመለስ ድምፃችንን በአንድነት እናሰማ!!
በተረፈ ወርቁ (ዲ/ን)

የኢትዮጵያ ታሪክ ትልቅ ባለውለታ የሆኑት የነፍሰ ኄር ፕ/ር ሪቻርድ ፓንክረስት ልጅ የሆኑት ዶ/ር አሉላ ፓንክረስት፤ በውጪ ሀገር የሚገኙ የኢትዮጵያ ቅርሶች አስመላሽ ኮሚቴ ሰብሳቢ በመሆን እየሠሩ ይገኛሉ፡፡ ባለፉት ጥቂት ዓመታትም በተለይ በመቅደላ ዘመቻ ወቅት በእንግሊዝና በሌሎች የአውሮፓ ሀገራት ተዘርፈው የተወሰዱ ቅርሶቻችንን በማስመለስ ረገድ ትልቅ ሥራ እየሠሩ ናቸው፡፡

በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ የኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ተቋም የሠራ ባልደረባ ነበርኩበት ጊዜ እንደማስታውሰውም፤ ወላጅ፣ አባታቸው ፕ/ር ሪቻርድ ፓንክረስት (ባለቤታቸው ሪታ ፓንክረስት)፣ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚደንት የነበሩት ፕ/ር አነድርያስ እሸቴ፣ የታሪክና የቅርስ ጥበቃ ምሁራን፣ የኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ወዳጆች ማኅበር፤ በሀገር ውስጥና በውጪ ሀገር በሚገኙ የኢትዮጵያ ታሪክና ቅርስ ተቆራቋሪ በሆኑ ወዳጆች በተቋቋመው AFROMET በተባለ ድርጅት አማካኝነት- የዐፄ ቴዎድርስ ክታብ፣ የጸሎት መጽሐፋቸው፣ ጎራዴያቸውና ሌሎች ቅርሶች ወደ ኢትዮጵያ ተመልሰው ነበር፡፡

እነዚህ በመቅደላው ዘመቻ ተዘርፈው ወደ እንግሊዝ ተወስደው የነበሩና የተመለሱ ብርቅዬና ውድ የሆኑ ቅርሶቻችንም በአንጋፋው የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፤ የኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ተቋም ቤተ-መዘክር ውስጥ ለሕዝብ ቀርበው እንደነበርም አስታውሳለሁ፡፡

ይህ የእነ ነፍሰ ኄር ፕ/ር ሪቻርድ ፓንክረስትና በሀገር ውስጥና በውጪ ሀገር ያሉ የኢትዮጵያ ታሪክና ቅርስ ተቆርቋሪዎች ጥረት ዛሬም ሳይቋረጥ- በፕ/ር ሪቻርድ ፓንከረስት ልጅ በሆኑት በዶ/ር አሉላ ፓንክረስት ቀጥሎ ባለፉት ጥቂት ወራትም በመቅደላ ዘመቻ የተዘረፉ ታቦታትን ጨምሮ የተለያዩ ቅርሶቻን ወደ ኢትዮጵያ እንዲመለሱ ተደርገዋል፡፡

ታቦታቱ በእንግሊዝ፣ የለንደን ቅድስት ማርያም ቤ/ክ በተደረገ መንፈሳዊ ሥነ-ሥርዓት ለቤተክርስቲያኒቱ እንዲመለስም ተደርጓል፡፡

ሌሎች ቅርሶቻችንም በኢትዮጵያ እንግሊዝ አምባሳደር በሆኑት አምባሳደር ተፈሪ፤ ለቅርስ ጥበቃ ባለ ሥልጣን በአካል ተገኝተው ማስረከባቸውን ከመገናኛ ብዙኃን ተከታትለናል፡፡ ይህ ብዙዎቻችንን ከልብ ያስደሰተ፤ ይበል የሚያሰኝ ሥራ ነው፡፡

ይሁን እንጂ ከሰሞኑን ደግሞ፤ ከመቅደላ የተዘረፈ እጅግ የተዋበና በልዩ ጥበብ የተሠራ ጋሻ በአንድ ግለሰብ አማካኝነት ለጨረታ መቅረቡን ዶ/ር አሉላ ገልጸውልኛል፡፡

ይህ የኢትዮጵያ ቅርስ የሆነ ጋሻ ወደ ሀገሩ እንዲመለስም የቅርስ ተቆርቋሪ የሆኑ ሁሉ በቲወተር (በኤክስ) እና በሌሎች ሶሻል ሚዲያ የትስስር ገጾች ድማፃችንን እንድናሰማ የቪዲዮ መልእከት አስተላልፈዋል፡፡

ይህ ቅርስ፣ ጋሻ የኢትዮጵያውያን፣ የአፍሪካና የመላው ጥቁር ሕዝቦች የነጻነት ተጋድሎ ትልቅ ትእምርት/ተምሳሌት ነው፡፡ ይህ ለጨረታ የቀረበውና ከ150 ዓመታት በላይ ያስቆጠረ ቅርስ ‹ጋሻ› በክብር ወደ ሀገሩ እንዲመለስ ለታሪካችንና ለቅርሶቻችን የምንቆረቆር ኢትዮጵያውን ሁሉ ድምፃችንን በአንድነት ሆነን ልናሰማ ይገባናል፡፡

ይህ የኢትዮጵያውያን ጥበብ የፈሰሰበትና እጅግ የተዋበ ቅርሳችን፤ ‹ጋሻ› የኢትዮጵያውያን፣ የአፍሪካና የመላው ጥቁር ሕዝቦች የነጻነት ተጋድሎ ትልቅ ትእምርት/ተምሳሌት ነው ስልም በምክንያት ነው፡፡

አውሮፓውያን ቅኝ ገዢ ኃይላት ጥቁር ሕዝብ ከእንሰሳ ያነሰ ስብእና ያለው፤ የራሱ ታሪክ፣ ሥልጣኔ፣ ዕድገት፣ ባህል… ወዘተ. የሌለው ብለው ድመድመው አፍሪካን እንደ ቅርጫ ሥጋ ተቀራምተው ሕዝቦቿን በባርነት ሲያግዙ በነበረበት ዘመን- አንድ የጥቁር ምድር/የሐበሻ ንጉሥ፤ የቋራው አንበሳ/ዐፄ ቴዎድሮስ የእንግሊዝንና የአውሮፓውያንን መልእክተኞች እግረ ሙቅ ውስጥ አስገብቶ ራሷን ታላቋ ብሪታንያ እያለች ከምትጠራውና የዓለም 1/3 በቅኝ ከምትገዛው ሀገር ጋር እኩል መደራደሪያ እድርገዋቸው ነበር፡፡

መላው አፍሪካና ጥቁር ሕዝብ በባርነትና በቅኝ ግዛት ቀምበር ስር ወድቆ ሲማቅቅ ነበረበት ወቅት የሐበሻው ጥቁር ንጉሥ፤ ዐፄ ቴዎድሮስ ሁላችንም በፈጣሪ ፊት እኩል ነን፤ በሚል መርሕ ራሳቸውን ከሁሉም በላይ ነን ብለው የሚያስቡትን አውሮፓውያንን/ነጮችን- በኢትዮጵያውያን የነጻነት እሳቤና ከፍ ባለ የመንፈስ ልእልና ድል በማድረግ ለአፍሪካና ለመላው ጥቁር ሕዝቦች የነጻነትና የጀግንነት ኩራት ሆነዋል፡፡

ይህ ከመቅዳላ ተዘርፎ ለጨረታ የቀረበው ቅርሳችን- ‹ጋሻ› የዚህ ኢትዮጵያዊነት የነጻነት እሳቤ፣ የሰው ልጆች እኩልነት መገለጫና የመንፈስ ልእልና ትእምርት/ምልክት ነውና ቅርሳችን ወደ ሀገሩ፤ ኢትዮጵያ እንዲመለስ፤ ከዶ/ር አሉላ ፓንክረስትና ኬሎች ሀገር ወዳድ ኢትዮጵያውያን ጋር በአንድነት ሆነን ድምፃችንን እናሰማ!!

የዶ/ር አሉላ ፓንክረስት ከመቅዳላ ተዘርፎ የነበረና ለጨረታ የቀረበውን ቅርሳችንን/ጋሻ  ወደ ሀገሩ እንዲመለስ ሁላችንም በጋራ ድምፃችንን እንድናሰማ የቪዲዮ መልእክት ያስተላለፉበት ሊንክ እንሆ!!

ሰላም ለኢትዮጵያ!!

 

https://youtu.be/kCNUOPwOKHE?si=asxKpqiewbFxtCR7
https://amharic.zehabesha.com/archives/189001

No comments:

Post a Comment

https://youtu.be/VUfa5eupQTc?si=Zm73w18dFB27xlqD       https://youtu.be/LcFmz2Xq5MY?si=7uP6VZsd2ksEulUf   https://youtu.be/7dUVmj8go7s?si=Px...