Sunday, September 24, 2023

የፋኖዎች ጎንደር መግባት እድምታዎች
 

ፋኖዎች ጎንደር ከተማ መስከረም 12 ቀን 2016 ዓ/ም መግባታቸው በስፋት እየተዘገበ ነው፡፡ እጅግ በጣም በርካታ የአገዛዙ ታጣቂዎች በሰልፍ እጅ ሰጥተዋል፡፡ ብዙዎችም ሙትና ቁስለኛ ሆነዋል፡፡ አገዛዙ መልሶ ጎንደር ከተማን ለመቆጣጠር ከነባህር ዳር ተጨማሪ ኃይል ወደ ጎንደር እየላኩ ነው፡፡ በአገዛዙ ሰዎች ዘንድ ከፍተኛ ድንጋጤ የፈጠረ ሲሆን፣ አገዛዙ ያወጀው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መክሸፉን በገሃድ ያመላከተ ነው፡፡ያለ ምንም ጥርጥር የአገዛዙ የጎንደር ሽንፈት፣ ጎንደር እጅግ በጣም ታሪካዊትና ወሳኝ ከተማ እንደመሆኗ፣ በአዲስ አበባ ፖለቲካውን በእጅጉ ነው የሚያናጋው፡፡

ሐምሌ 28 ቀን 2015 ዓ/ም ነበር አገዛዙ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ያወጀው፡፡ የኦህዴድ መካናይዝድ ጦር ፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድንም ሳይቀር ተጠቅሞ፣ በአይሮፕላን መሳሪያዎችና ታጣቂዎች በማመላለስ፣ በትላልቅ ከተሞች ውስጥ ውጊያ ከፈተ፡፡ ያለ የሌላ ኃይሉን ተጠቅሞ፡፡ ታንኮችንና መድፎችን፣ እንደ ፋሲል ግንብ ባሉ ቅርሶችና አብያተክርስቲያናት፣ ፎቆች ፣ የንግድ እንቅስቃሴዎች ያሉባቸው ከተማዎች መሃል በማድረግ፡፡

ፋኖዎች በከተሞች ውድመት እንዳይከተል፣ ታክቲካል ማፈግፈግ አድርገው ከተሞችን ለቀው ወጡ፡፡ አገዛዙ ተዋግቶ የገባ ይመስል፣ መዋሸትና ማተለል ባህሪው ስለሆነ፣ ጎንደር፣ ባህር ዳር፣ ደብረ ማርቆስ፣ ደብረ ብርሃን፣ ሸዋ ሮቢትንና ላሊበላን ከተማ ከዘራፊዎች ተቆጣጠርኩ ብሎ መለፈፍ ጀመረ፡፡ ፋኖዎች የአገዛዙ ጦር ከከተሞች ውጭ በነጻነት እንዳይንቀሳቀስ አደረጉት፡፡ የአገዛዙ ጦር ከሎጂስቲክ፣ ከስንቅ፣ ከትጥቅ አንጻር ከፍተኛ ችግር ውስጥ ገባ፡፡ ብዙዎች አንዋጋም እያሉ እጅ መስጠት ጀመሩ፡፡ በደፈጣ ውጊያዎችን ብዙዎች አለቁ፡፡ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት በአማራ ክልል የገባው የአገዛዙ ጦር 40% ከጥቅም ውጭ እንደሆነ ነው፡፡

v

አገዛዙ በተቆጣጠራቸው ከተሞች፣ ሴቶችን መድፈር፣ ዜጎችን ማሰር፣ ወጣቶችን መረሸን የቀን ተቀን ተግባሩ ሆነ፡፡ ያ መቆም ስላለበት፣ መስከረም 3 ቀን 2016 ዓ/ም ሁለተኛ ዙር የማጥቃት ኦፐሬሽን በፋኖዎች ተጀመሩ፡፡ አገዛዙ ዘራፊ ካላቸው ፋኖዎች አስለቀኩ ባላቸው ስድስት ከተሞች ውስጥ በሶስቱ ፣ በጎንደር፣ በደብረ ማርቆስና በሸዋ ሮቢት፣ በተጨማሪም በቆቦ፣ በደብረ ታቦር ፋኖዎች ገብተዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት በወልዲያ፣ በላሊበላ፣ በሃይቅ፣ በኩታበር፣ በምንጃር አረርቲ ዙሪያ ከፍተኛ እንቅስቃሴዎች ያለ ሲሆን፣ በአስተማማኝ ሁኔታ በአገዛዙ ስር የነበረችው ደሴም በአቅራቢዋ የተኩስ ድምጽ እየሰማች ነው፡፡

አገዛዙ ተጨማሪ ኃይል ማሰለፍ ስላልቻለ፣ ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ ታጣቂዎችን ማዘዋወር ጀምሯል፡፡

በተለይም በምንጃር የተጀመረው የፋኖዎች እንቅስቃሴ አገዛዙን ከስሩ ነው ያናጋው፡፡ ፋኖዎች ምንጃርን ሲቆጣጠሩ፣ አገዛዙ ከፍተኛ ሰራዊት አሰማራ፤ መልሶ ምንጃርን ለመያዝ፡፡ ሽንፈት አጋጠመው፡፡ አልቻለም፡፡ ፋኖዎች በኦሮሞ ክልል ኢጄሬ ድረስ ዘልቀው በመግባት የብልጽግና ጦርን አሳደዱ፡፡ ከተለያዩ ግንባሮች በማምጣት፣ እንደገና ከ15 ሺህ በላይ በታንክ የታገዘ ውጊያ አገዛዙ ከፈተ፡፡ አሁንም አልቻለም፡፡ ተሸነፈ፡፡ ለሶስተኛ ጊዜ ኃይል አጠናክሮ በዋና መንገዶች መጣ፡፡ በከተሞች ላይ ጉዳት እንዳይደርስ፣ ፋኖዎች ከከተሞች አፈገፈጉ፡፡እንዳለ ወጣቱ ጫካ ገባ፡፡ ሆኖም ምንጃር የገባው ሜካናይዝድ ጦር ፋታ አላገኘም፡፡ በሁሉም አቅጣጫ በደፈጣ የአገዛዙ ታጣቂዎች ሙትና ቁስለኛ እየሆኑ ነው፡፡

እንግዲህ መጠየቅ ያለበት፣ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ፋኖን በተመለከተ ምን ውጤት አመጣ የሚለውን ጥያቄ ነው፡፡ ብዙዎቻችን ከጅምሩ ፋኖ የህዝብ ልጅ ነው፡፡ ህዝብን ደግሞ ማሸነፍ አይቻልም" ብለን ስንመክርና ስናስጠነቅቅ ነበር፡፡ሰዎቹ ግን ሊሰሙ አልቻሉም፡፡ ጥጋብ ስላወራቸው፣ የማያሸንፉትን ጦርነት ለኩሰው፣ የነርሱን ልጆች ውጭ አገር ልከው፣ የድሃውን ልጅ እያስፈጁ ነው፡፡

ግርማ ካሳ
https://amharic-zehabesha.com/archives/186028

No comments:

Post a Comment

https://youtu.be/VUfa5eupQTc?si=Zm73w18dFB27xlqD       https://youtu.be/LcFmz2Xq5MY?si=7uP6VZsd2ksEulUf   https://youtu.be/7dUVmj8go7s?si=Px...