Wednesday, April 26, 2023

በአገራችን ምድር የሚካሄደው ሁለ-ገብ ጦርነት የውክልና ጦርነት ነው!!   ጦርነቱ የአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝምና የግብረ-አበሮቹ ነው!
 

ፈቃዱ በቀለ (ዶ/ር)

ሚያዚያ  25፣ 2023

መግቢያ

ህወሃት ወይም ወያኔ የኢትዮጵያን ህዝብ የመኖርና ያለመኖር ዕድል 27 ዓመታት ያህል ስልጣን ላይ በቆየበት ጊዜ ሲወስን፣ ቀጥሎ ስልጣንን የጨበጠው የኦርሞን የበላይነት አሰፍናለሁ ብሎ አገርን የሚያተረማምሰው የአቢይ አህመድና የሺመልስ አብዲሳ አገዛዝ አገራችን እንድትንኮንታኮት፣ ህዝባችን ደግሞ በጎሳና በሃይማኖት ተሳቦ በሚካሄድ ጦርነት የእርስ በርስ ጦርነት በማካሄድ አቅጣጫው እንዲጠፋበትና ኃይሉም ተሟጥቶ እንዲቀር የማይሰሩት ተንኮልና ወንጀል ይህ ነው አይባልም። ከአንድ ብሄረሰብ የተውጣጣው ወያኔ የሚባለው የወንበዴ ድርጅት እራሱን “የነፃ አውጭ” ድርጅት ብሎ በመጥራት አገራችንን በጎሳ በመከለልና በመከፋፈል ዘረፋ ሲያካሂድና አገርን ሲያተረማምስ እንደነበር ይታወቃል። ሀወሃት በነፃነት ስም ጦርነትን ሲያካሂድና ስልጣንን ከጨበጠ በኋላም የትግሬን ብሄረሰብ ጥቅም አስጠብቃለሁ ቢልም በመሰረቱ የአሜሪካንና የግብረአበሮቹን አገርን የመበታተንና ህዝብን የማዳከም ጥቅም ብቻ ነበር ያስጠብቅ የነበረው። ስለሆነም በአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም፣ በአውሮፓ አንድነትና በወያኔ መሀከል በነበረው የጥቅም ግኑኘት የተነሳ  አገራችን ከውስጥ እንድትቦረቦር በማድረግ ከውጭ ለሚመጣ ወራሪ ኃይል እንድትጋለጥ ለማድረግ በቃ። በተለይም ተግባራዊ ባደረገው የኒዎ-ሊበራል ኢኮኖሚ ፖሊሲ አማካይነት ከፍተኛ የባህል ውድመት በማድረስ፣ በዶላር የሚታለልና በቀላሉ ለአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም ለመንበርከክ ዝግጁ የሆነ አዲስ የህብረተሰብ ክፍል ብቅ እንዲል አደረገ።  ወያኔ ስልጣን ላይ በቆየበት ጊዜ የአብዮታዊ ዲሞክራሲያዊ ፖለቲካን እከተላለሁ ቢልም በመሰረቱ ከዚህ አስተሳሰብ ጋር ምንም የሚያገናኘው ነገር አልነበረም። በመለስ ዜናዊ ይመራ የነበረው የህወሃት አገዛዝ የተሰማራው የአገሪቱን ሀብት በመዝረፍ እንጂ በኢንዱስትሪ ተከላና በቴክኖሎጂ ፈጠራ ላይ ሊሰማራ የሚችል ኃይል ለመፍጠር አልነበረም ዋና ዓላማው።  ስለሆነም ህወሃት ተግባራዊ ባደረገው የኒዎ-ሊበራል ኢኮኖሚ ፖሊስ አማካይነት በዘረፋ የተሰማሩ የናጠጡ ቱጃሮች ብቅ ከማለታቸው በስተቀር ወደ ውስጥ ያተኮረ፣ በሳይንስና በቴክኖሎጂ ላይ የተመሰረተና ለሰፊው ህዝብ የስራ መስክ ሊከፍት የሚችል ሰፋ ያለ የአገር ውስጥ ገበያ ሊገነባ አልቻለም።

ካለፉት አምስት ዓመታት ጀምሮ ደግሞ ስልጣንን የተቆናጠጠው በአቢይ አህመድ የሚመራው የኦሮሙማ አገዛዝ በመሰረቱ በሌላ ሽፋን ስም የወያኔን ፈለግ በመከተል ነው ብዝበዛና ዘረፋ የሚያካሄደውና በህዝባችንም ላይ ሁለ-ገብ የሆነ ጦርነትን የከፈተው። ይህም ማለት አቢይና አገዛዙም ልክ እንደወያኔው የዘረፋና የከፋፍለህ ግዛው አገዛዝ የአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝምንና የግብረአበሮቹን ጥቅም የሚያስጠብቁ ናቸው ማለት ይቻላል። ይህም ማለት ወያኔ የሰፊውን የትግሬን ብሄረሰብ ጥቅም ያላስጠበቀውን ያህልንና ከድህነትም እንዲላቀቅ ያላደረገውን ያህል፣ የአቢይ አህመድና የሺመልስ አብዲሳ ቡድንም ከድህነትና ከኋላ-ቀርነት ለመላቀቅ የሚፈልገውን ሰፊውን የኦሮሞ ብሄረሰብ ጥቅም የሚያስጠብቅ አይደለም።  ስለሆነም በተለይም አቢይ አህመድ በዓለም አቀፍ የአገዛዝ ሂራርኪ ውስጥ በመካተትና የአሜሪካንን ኢምፔሪያሊዝምን የአገር አፍራሽነት ሴራንና ህዝብን የመበታተን ፍላጎት በማስጠበቅ አገራችንን ከፍተኛ አደጋ ውስጥ ከቷታል ማለት ይቻላል። ወያኔ ነፃ አውጭ ነን ባዮች ሌሎች የብሄረሰብ ኢሊቶችን በስሩ በማሰባሰብና የእርስ በርስ ጦርነት በመቀስቀስና በመዝረፍ የአገራችንን ታሪክ፣ ባህሉን፣ ማህበረሰብአዊ ግኑኝነቱንና ስነ-ልቦናውን በመበወዝ አዲስ የታሪክ ምዕራፍ ሰርቷል፤ ወይንም የአገራችን ታሪክ በአዲስ መልክ እንዲጻፍ ለማድረግ ሞክሯል። የኦሮሙማው የአቢይ አገዛዝ ደግሞ ሁሉንም በመሰልቀጥና ግዛትን በማስፋፋት የኦሮሞን የበላይነት አሰፍናለሁ በማለት እዚህና እዚያ ሲንቀጀቀጅ ይታያል፤ በሁሉም አቅጣጫ ጦርነት በመክፈት ህዝባችንን መቆሚያና መቀመጫ አሳጥቶታል። ይሁንና ግን አቢይ አህመድና ግብረ-አበሮቹ የኦሮሙማን የበላይነት ለማስፈን ሳይሆን የሚሰሩት በቀጥታ የአሜሪካንን ትዕዛዝ በመቀበል ኢትዮጵያ ከውስጥ እንድትዳከምና እንድትከፋፈል ማድረግ ነው። የተከፋፈለና የተዳከመ ህዝብ ደግሞ ጠንካራ ኢኮኖሚ ለመገንባት ስለማይችል በተለያዩ ኢሌቶች መሀከል በሚፈጠር የስልጣንና የሀብት ሽኩቻ በጦርነት ውስጥ በመዝፈቅ ልጆቹን ሲገብር ይኖራል። ባጭሩ በጋራ በመነሳት አገሩን እንዳይገነባ ይደረጋል ማለት ነው። በዚህ መልክ በማወቅም ሆነ ባለማወቅ የውጭ ኃይሎችን ጥቅም ለማስጠበቅ በሚካሄድ ዘረፋና የእርስ በርስ ጦርነት ሰፊው ህዝባችን እፎይ ብሎ እንዳይኖር ማድረግ ብቻ ሳይሆን፣ አገራችንና ህዝባችን ቆርቁዘውና ደሃ ሆነው ለብዙ ዓመታት እየተሰቃዩ ይኖራሉ። የአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝምም ዋናው ዓላማ እንደ ኢትዮጵያ የመሰለች የብዙ ሺህ ዓመታት ታሪክና ሰፊውን ህዝብ የሚያስተሳስር ባህል ያላትን አገር አዳክሞና በታትኖ ሰፊው ህዝብ አቅጣጫው ጠፍቶበት ተበታትኖ እንዲቀር ማድረግ ነው። በሌላ አነጋገር፣ የሃይቲው ዐይነት ሁኔታም በአገራችንም ምድር መፈጠር አለበት። ምናልባትም ማፊያዊ የሚመስሉ ቡዱኖች በመፈጠር አገራችንን ሲያምሱና ምስኪኑን ህዝባችንን ደግሞ  በሰላም እንዳይኖር ያደርጉታል። ይህ ዐይነቱ ነው የታላቁ አሜሪካ የውጭ ፖለቲካ ስልትና ስትራቴጂ።

ቀደም ብሎ የህውሃትን አገዛዝ አነሳስ፣ ምንነትና ተግባር በሚመለከት ከተለያዩ የኢትዮጵያ የፖለቲካ ተዋንያንና ጋዜጠኞች የሚቀርቡትን ገለፃዎች በምንመረምርበት ጊዜ በሳይንስ አነጋገር፣ ገለፃ(Descriptive) እየተባለ የሚጠራው አቀራረብ እንጂ፣ ሳይንሳዊ ትንተና እንዳልሆነ ግልጽ ነው። ገለፃ ነው የሚያሰኘው ማንኛውም ሰው የሚያውቀውን በጽሁፍ ወይም በዜና መልክ ማቅረቡ ሲሆን፣ ውስጣዊ ይዘቱን፣ የርዕዮተ-ዓለም መሰረቱንና ከዓለም አቀፍ የብዝበዛ፣ የፀረ-ዕድገትና የጭቆና አገዛዝ አወቃቀር ተዋረድ( World governance or military industrial complex hierarchy)ጋር የተያያዘ መሆኑን በመመርመር ስለማይጻፍ ነው። የፖለቲካውን ሜዳ እንደዚህ ዐይነቱን ፊዩዳላዊ አቀራረቦች ወጥረው ስለያዙት 27 ዓመት ያህልም ሆነ ከዚያ በፊት በተለይም በአብዮቱ ወቅት የተካሄደውን የፖለቲካ ቲያትር በሳይንስ፣ በፍልስፍናና በቲዎሪ መልክ በማገናዘብና ተጨባጭ ድርጊቶችን በመተርጎም ለመተንተንና ለማሳመን እጅግ አስቸጋሪ እየሆነ መጥቷል። አቢይ አህመድና ግብረ-አበሮቹ ስልጣን ላይ ሲወጡም የውጭ ኃይሎች በስተጀርባው እንዳሉበት ስለማይታወቅ፣ ቢታወቅም እንኳን ደፍሮ ለመናገር የሚችል ሰው ወይም ድርጅት ባለመኖሩ አቢይ አህመድና ጓደኞቹ በህዝባችን ላይ የሚሰሯቸው ወንጀሎች፣ የሚከተሉት የኢኮኖሚ ፖሊሲ በእነሱ እንደተቀነባበረ ተደርጎ ነው የሚቀርበው። ስለሆነም የአቢይ አህመድን አገዛዝ የሚወነጅሉ ግለሰቦችም ሆነ ይህንን ወይም ያኛውን ድርጅት እንወክላለን የሚሉ ግለሰቦች የሚሰሩት የታሪክ  ወንጀል የአሜሪካንንን ኢምፔሪያሊዝምና ግብረ-አበሮቹን ከደሙ ንጹህ በማድረግ እነሱን በመለማመጥ ታዳጊውን ወጣት ማሳሳት ነው። በተለይም ሰሞኑን በአንዳንድ ኢትዮጵያውያን የጦር መኮንኖች የሚሰጠው የተዘበራረቀ ገለጻ በኢትዮጵያ ውስጥ በተንሰራፋው የውንብድና ፖለቲካ የአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝምና ግብረ-አበሮቹ እጃቸው እንደሌለበት ነው።  በነዚህ የፖለቲካ ተዋንያን ዕምነትም አሜሪካ የኢትዮጵያ ህልውና በጥያቄ ውስጥ እንዲገባ፣ አገሪቱም እንድትፈራርስ አይፈልግም የሚል ነው። በጭንቅላቱ የቆመ አዲስ ቲዎሪ እያስተማሩነ ነው መለት ነው። ቀድሞ ህወሃት፣ አሁን ደግሞ አቢይ አህመድና ግብረ-አበሮች በራሳቸው ስሜትና አስተሳሰብ በመነሳት ብቻ ነው አገራችንን እያፈራርሱና በህዝባችን ላይ ጦርነት በማወጅ ህዝባችንን ፍዳውን የሚያሳዩት ብለው ነው  የሚነግሩን። በአቋራጭ ስልጣን ለመውጣት የሚፈልጉ እነዚህን የመሳሰሉ ኃይሎች ከሚታዩና ከተጨባች ሁኔታዎች በመነሳት ሳይሆን ነገሮችን ሸፋፍነው በማቅረብና የአሜሪካንን ኢምፔሪያሊዝም ከደሙ ንጹህ አድርጎ በማቅረብ ለዕውነተኛ ነፃነትና ዲሞክራሲ፣ እንዲሁም ለተሟላ ዕድገት  ለሚደረገው በዕውቀት ላይ ለተደገፈ ትግል እንቅፋት በመሆን ላይ ናቸው።

እንደሚታወቀው እንደኛ ባለው አገር ውስጥ የሚከሰቱና የሚያድጉ የፖለቲካ ሁኔታዎች ከሰማይ ዱብ የሚሉ ሳይሆኑ፣ በተለይም በዛሬው ዓለም የዚያው አገር ህብረተሰብአዊ አወቃቀርና ዓለም አቀፋዊ የፖለቲካ አገዛዝና ሁኔታ ውጤቶች ናቸው ማለት ይቻላል። ከ1940ዎች መጨረሻ ጀምሮ በአገራችን ምድር የተዋቀረውን የመንግስት መኪናና አገዛዝ፣ የፖለቲካ ግንዛቤ፣ የኢኮኖሚና የማህበራዊ ግኑኝነት፣ እንዲሁም የባህልና የስነ-ልቦና አቀራረጽ በምንመረምርበት ጊዜ በአገራችን የታሪክ ሂደት ውስጥ፣ የመዘበራረቅ ሁኔታና ራስን በራስ ያለማግኘት ጉዳይ የዓለም አቀፍ ኢኮኖሚ አወቃቀር፣ የፖለቲካ፣ የሚሊታሪና የፀጥታ ጉዳይ ወሳኝ ሚናን እንደተጫወቱና እንደሚጫወቱ መገንዘብ እንችላለን። በሌላ አነጋገር፣ ከ1940ዎቹ ዓመታት መጨረሻ ጀምሮ በተለያየ መልክ የሚገለጸው የአገራችን ሁኔታ በውስጣዊ ኃይል ንቃተ-ህሊና የሚወሰንና የሚታቀድ ሳይሆን በውጭው ዓለም እንደተወሰነና እንደሚወሰን በሳይንስና በቲዎሪ ማረጋገጥ ይቻላል።  ካፒታሊዝም በተንጠባጠበ መልክ ሲገባና በተለይም የተወሰነውን የህብረተሰብ ክፍል የፍጆታ አጠቃቀምና ባህላዊ ሁኔታ ሲለውጥ በፖለቲካው መስክም ላይ የበኩሉን አስተዋጽዖ ለማድረግ ችሏል። እንደዚሁም የሚሊታሪው፣ የጸጥታው፣ የፖሊሲና የሲቪል ቢሮክራሲው፣ እነዚህ ሁሉ ከረጅም ጊዜ አንስቶ ሲወርድ ሲዋርድ በመጣና በዳበረ ዕውቀት የታነፁ ሳይሆን አነሰም በዛም የግሎባል ካፒታሊዝምና የአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም ውጤቶች በመሆናቸው ይሰሩ የነበረው አገራችንን በጸና መሰረት ላይ ለመገንባትና ለመጭው ትውልድ ማስተላለፍ ሳይሆን አውቀውም ሆነ ሳያውቁ ይሰሩ የነበረው ለአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም ነበር ማለት ይቻላል። እነዚህ ደግሞ የግዴታ በመንግስት ፖሊሲና የአስራር ሁኔታና የዕድገት ጉዳይ ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ ነበራቸው። በአፄ ኃይለስላሴ የአገዛዝ ዘመን ተግባራዊ የሆነውን የኢኮኖሚ ፖሊሲ በምንመረምርበት ጊዜ በቀጥታ ከውጭ ረቆ የመጣ ሲሆን፣ በማኑፋክቸሪንግ ላይ የተመሰረተና ሰፋ ላለ  የገበያ ኢኮኖሚ ግንባታ የሚያመች አልነበረም። ይህ ዐይነቱ ሳይንሳዊና ሁለ-ገብ ባህርይ የሌለው የኢኮኖሚ ፖሊሲ በአገራችን ምድር ውስጥ ዝብርቅርቅ ሁኔታንና የተሙለጨለጨ የህብረተሰብ ክፍል  በመፍጠር፣ በዚያው መጠንም ለተገንጣይ ኃይሎች አመቺን ሁኔታ ሊፈጥር ቻለ። በሌላ አነጋገር፣ የብሄረሰብ እንቅስቃሴ ቀስ በቀስ እያለ እያደገ የመጣው በአገራችን ምድር ብሄራዊ ባህርይ ያለውና የተስተካከለ ዕድገት ተግባራዊ ለመሆን ባለመቻሉ ነው። በሌላ ወገን ግን በጊዜው ተግባራዊ የሆነው የኢኮኖሚ ፖሊሲ አንድን ብሄረሰብ ብቻ ለመጥቀም ተብሎ ተግባራዊ የሆነ የኢኮኖሚ ፖሊሲ እንዳልነበር ሁኔታውን የመረመረ ሊገነዘበው ይችላል።

ከዚህ ሀቅ ስንነሳ የአገራችን ህልውና መዳከም መሰረቱ የተጣለው በአፄ ኃይለስላሴ ዘመን ነበር ማለት ይቻላል። ለዚህ ምሳሌ የሚሆነን የአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም ኤምባሲ ህንፃ እንዲስራ አንድ ጋሻ ያህል መሬት የተሰጠው ሲሆን፣ በአስመራ ደግሞ የቃኘው የጦር ካምፕ እንዲገነባ የተሰጠው ሰፊ መሬት የአገራችንን ህልውና አደጋ ላይ የጣለና ስትራቴጂያዊ በሆነ መልክ ሳይታሰብ አሜሪካንን እንደ አጋር አገር አድርጎ በማየት የተነሳ ነው። ይህ ዐይነቱ ከፊዩዳላዊ አስተሳሰበ የመነጨ የየዋህነት ፖለቲካ በቀላሉ ልንላቀቀው  የማንችለው ውስብስብ ሁኔታ ውስጥ ሲከተን፣ የአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም ደካማ ጎናችንን በመጠቀም ከዚኸኛውና ከዚያኛው የተውጣጡ የየብሄረሰቡን ኤሊቶች በመመልመል አጠቃላይ ጦርነት እንዲያውጁብን አመቺ ሁኒታን ፈጥሮላቸዋል። በአፄው ዘመን ይካሄድ የነበረው ፖለቲካ ከሳይንስ አንፃር ፖለቲካ ተብሎ ሊጠራ የሚያስችለው አንዳችም ነገር ስላልነበር በአገራችን ምድር መንፈሱ የጠነከረና ስትራቴጂካዊ በሆነ መንገድ ሊያስብ የሚችል የህብረተሰብ ክፍል ለመፈጠር አልተቻለም። የጠለቀ አስተሳስብ ያለውና አገር ወዳድ የሆነ ምሁራዊ ኃይል ለመፈጠር ባለመቻሉ አገራችን ከውስጥም ሆነ ከውጭ በተቀነባበረ መልክ የምትቦረቦርበትና የምትዳከምበት ሁኔታ ሊፈጠር ቻለ። ይህም ማለት ኢትዮጵያ የዛሬው አጅግ አደገኛ የሆነ የህልውና አደጋ ውስጥ ለመውደቅ የቻለችው የተለያዩ ኃይሎች በማወቅም ሆን ባለማወቅ የአሜሪካንን ኢምፔሪያሊዝም እንደ ነፍሰ-አባታቸው በማየታቸውና ሰፊውን ህዝብ ከድህነትና ከኋላ-ቀርነት ሁኔታ ውስጥ ሊያላቅቀው የሚችል ሁለ-ገብ የሆነ የኢኮኖሚና የማህበራዊ ፖሊሲ ባለመከተላቸው ነው። በተጨማሪም አንድ አገር ከታች ወደ ላይ ቀስ በቀስ እንዴት እንደሚገነባና ህብረተሰቡ ርስ በርሱ እንዲተሳሰር የባህል ጥገናዊ ለውጥ ተግባራዊ ለማድረግ ባለመቻላቸውና ልዩ ልዩ ተቋማትን ለመገንባት የወሰዱት እርምጃ ባለመኖሩ ነው።

ስለሆነም ባለፉት ስድሳ ዓመታት በንቃተ-ህሊና ጉድለት ወይም በአዕምሮ አለመብሰል ምክንያት የተነሳ ተማርኩኝ የሚለውና በተለያዩ ጊዜያት በመንግስት መኪና ላይ ቁጥጥ ያሉ አገዛዞች አውቀውም ሆነ ሳያውቁ ፀረ-ዕድገትና ፀረ ህዝብ ፖሊሲና ፖለቲካ በመከተላቸው የአስተሳሰብ መዘበራረቅና የእርስ በእርስ ሽኩቻ ተፈጥሯል። ሃሳብን የሚሰበስብና ለጋራ ዓላማ እንድንታገል የሚያደርግ ፍልስፍና ወይም ርዕይ ለመዳበር ባለመቻሉ፣ በተለይም የቢሮክራሲው፣ የተወሰነው የሚሊታሪና የፀጥታው ኃይል የዚህ ወይም የዚያኛው የውጭ የስለላ ድርጅት ሰለባ በመሆን አገራችንን ወደ ጦር አውድማነት ሊለውጣት የሚያስችሉ ሁኔታን አመቻችተዋል።  ይህ እየተደራረበና እየተወሳሰበ የመጣ ጉዳይ ዛሬ አገራችን ለምትገኝበት ሁኔታ ዋናው ምክንያት ነው ማለት ይቻላል። በሌላ ወገን የወጭው ኃይል ሰለባ ያልሆኑ  ቀድሞ እንደሶብየት ህብረት፣ ጃፓንና ደቡብ ኮሪያ፣ እንዲሁም ቻይና ጠንካራ ኢኮኖሚና ባህል በመገንባት ራሳቸውን ነፃ ማድረጋቸው ብቻ ሳይሆን መፈራትና መከበር ችለዋል። ህዝባቸውም በሄዱበት ሁሉ የሚከበሩ ለመሆን በቅተዋል። ቻይና ደግሞ አሜሪካንን ለመተካት የምትችል ኃያል መንግስት ለመሆን በመገስገስ ላይ ናት። በአንፃሩ ግን የሶስት ሺህ ዘመን ታሪክ አላት የምትባል አገር እጅግ የደቀቀና በሁሉም አቅጣጫ  ለማሰብ በማይችል ጭንቅላት አገዛዞች እየተረበሽችና፣  በተለይም ደሃው ህዝብና ወጣቱ የጦርነት ሰለባ ለመሆን በቅተዋል።

ከዚህ ስንነሳ የወያኔን አነሳስና የኋላ ኋላ ስልጣን ላይ ወጥቶ የአገራችንን ዕድል 27 ዓመታት ያህል መደንገጉና ታሪክን ማበላሸቱ፣ ወይም ታሪካችን በአዲስ መልክ እንዲጻፍ ማድረጉ የተለያዩ የኢትዮጵያ ኃይሎችም ከውጭው ዓለም በተለይም ከአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም ጋር ባላቸው የቀረበና የተቆላለፈ ግኑኝነት አማካይነት ነው። ከዚህ ውጭ ማሰብና እስከዛሬ ድረስ በአገራችን ምድርና በህዝባችን ላይ የደረሰውንና የሚደርሰውን ሰቆቃና መሰደድ የወያኔ ድርጊት ብቻ አድርጎ ማቅረብ አላዋቂነት ብቻ ሳይሆን ከፖለቲካ ሳይንስ የአቀራረብና የአተናተን ዘዴ አንፃር ስንመረምረው የተሳሳተ አመለካከትና አቀራረብ ነው። በተጨማሪም በተለይም ከ1945 ዓ.ም በኋላ በዓለም አቀፍ ላይ ብቅ ያለው የኃይል አሰላለፍ  እንደኛ ባለው አገር ላይ ሊኖረው የሚችለውን አሉታዊ ተፅዕኖ ለመረዳት አለመቻል ነው። ስለሆነም ካለብዙ ምርምር ከውጭ የኮረጅነው ትምህርት በዲሲፕሊንና በጥሩ ርዕይ የሚመራና የሃሳብ ጥራትነት የሚኖረው አዲስ ትውልድ እንዲፈጠር ለማድረግ አለመቻሉ ብቻ ሳይሆን፣ በተለይም ደግሞ ከአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም ጋር የነበረን የጠበቀ ግኑኘነትና በፖሊሲ አውጭው በቢሮክራሲው ላይ ከፍተኛ የሆነ አሉታዊ ተፅዕኖ ማሳደሩ አገራችንና ህዝባችን የሳይንስና የቴክኖሎጂ ባለቤት እንዳይሆኑ ለማድረግ በቅቷል። አንድ አገር ከታች ወደ ላይ የሚያድግ በሳይንስና በቴክኖሎጂ የሚደገፍ ኢኮኖሚ ከሌላት ደግሞ ህዝቧን ከድህነትና ከረሃብ ለማላቀቅ በፍጹም አትችልም ማለት ነው።

አቢይ አህመድና አገዛዙ፣ በተጨማሪም የአማራን ክልል እንወክላለን ብለው አገራችንን የሚያተረማምሱት ኃይሎች በሙሉ በዚህ ዐይነቱ የተበላሽ ሁኔታ ውስጥ  የተፈጠሩና ያደጉ  ህሊና ቢሶች ለመሆን የበቁ ናቸው። ጭንቅላታቸውን ለማዳበርና በሁሉም አቅጣጫ ለማየት እንዲችሉ ጠለቅ ያለና ሁለ-ገብ ዕውቀት ያልቀሰሙ በመሆናቸው የአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም ታዛዥ በመሆን አገራችንን ለመሰነጣጠቅ ሽር ጉድ ሲሉ ይታያሉ። አቢይ አህመድም ሆነ የአማራ ክልል መሪዎች ነን የሚሉት የወያኔን ጡት ሲጠቡ ያደጉ በመሆናቸው የሚያካሂዱት ፖለቲካ በሙሉ በአጠቃላይ ሲታይ ክልሉንና አገራችንን ያዳከመና ሊበታትንም የሚችል ነው። አቢይ አህመድም ሆነ እነዚህና ሌሎች የኒዎ-ሊበራል ኢኮኖሚ አቀንቃኞች ስለማህበረሰብና ስለህብረተሰብ ዕድገት የሚያውቁት ነገር ስለሌለ በቀላሉ ለውጭ ኃይሎች የሚያጎበድዱ ናቸው። በዝቅተኛ ስሜት በመመራትና ትዕዛዝ በመቀበል ለብሄራዊ ነፃነት በሚታገሉ ኃይሎች ላይ ጦርነትን  ያወጁ ናቸው። ባጭሩ ወያኔም ሆነ የአቢይ አህመድ አገዛዝ በህዝባችንና በአገራችን ላይ፣ በተለይም ደግሞ በአማራው ወገናችን ላይ የከፈቱት ጦርነት በአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም የሚደገፍ ነው። ይህም ማለት፣ ሁለቱም ኃይሎች፣ ህወሃትም ሆነ አቢይ አህመድና አጋሮቹ የሰፊውን የትግሬና የኦሮሞ ብሄረሰብ ጥቅም የሚያስጠብቁ አይደሉም። የሚያካሂዱትም ጦርነት የውክልና ጦርነት ስለሆነ በአገራችንና በህዝባችን ላይ ብቻ የታወጀ ሳይሆን በጠቅላላው የጥቁር አፍሪካ ህዝብም ላይ ነው። የአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም ከቻይና ጋር በገባው የጥሬ-ሀብት መቀራመት ፉክክርና የበላይነቴን አጣለሁ በማለት በሚያካሂደው ድብቅና የይፋ ጦርነት ወያኔንና አቢይ አህመድን በመጠቀም ጠቅላላውን አገራችንን ወደ ጦር አውድማነት በመለወጥ ላይ ይገኛል። ከዚህ ሀቅ ስንነሳ በተለይም ወጣቱ የትግሬና የኦሮሞ ብሄረሰብ ተወላጆች ቆም ብለው በማሰብ ከእንደዚህ ዐይነቱ የወያኔና የአቢይ አህመድና የግብረ-አበሮቹ ሴራ በመቆጠብ ከጠቅላላው ህዝባችን ጎን በመቆም ለዕውነተኛ ነፃነትና ዲሞክራሲያዊ መብቶች መታገል አለባቸው። ዕውነተኛ ነፃነታቸውንም ለመጎናጸፍ የሚችሉት እኔ ትግሬ ወይም ኦሮሞ ነኝ ብለው የመለየት አስተሳሰብን ሲያራምዱ ሳይሆን ከጠቅላላው የኢትዮጵያ ወጣት ጋር በመሰለፍ ብቻ ነው። ይህንን ለማድረግ የሚፈልጉ ከሆነ ደግሞ ራሳቸውን ማወቅ አለባቸው። ራሳቸውን ለማወቅ ደግሞ ከዕውነተኛ ዕውቀትና ጭንቅላትን በጥሩ መልክ ከሚኮተኩት ዕውቀት ጋር መተዋወቅ አለባቸው። አንድ ሰው ሰው መሆኑን የሚገነዘበው ጭንቅላቱ በትክክለኛ ዕውቀት ሲኮተኮት ብቻ ነው። ስለሆነም አገራችንን ከውድመት አድኖ ጠንካራና የምትከበር አገር እንድትሆን የሚፈልግ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ሁሉ የግዴታ መንፈሱን በትክክለኛ ዕውቀት ማነጽ አለበት። ይህ ሲሆን ብቻ ነው ራስን በራስ አግኝቶና ታሪክን ሰርቶ ለተከታታዩ ትውልድ ማስተላለፍ የሚቻለው።

ይህንን የአሰራር ስልት ወይም ሳይንሳዊ አቀራረብ መሰረት በማድረግ ነው የወያኔ አገዛዝንም ሆነ አሁን ደግሞ ህዝባችንን የሚያተረማምሰውንና ፋሺሽታዊ የሆነውን የአቢይ አህመድን አገዛዝ ምንነት ለመመርመር የምንችለው። ወያኔ በዓለም አቀፍ የአገዛዝ ሂራርኪ ውስጥ በመካተት ሀብትን ሲዘርፍና አገርን ሲያውድም የህወሃትን ጡት ሲጠቡ ያደጉት እነ አቢይ አህመድና ሺመልስ አብዲሳ የመሳሳሉት ባህለ-ቢስ ኃይሎች ከወያኔ የተሻለ ፖለቲካና የኢኮኖሚ ፖሊሲ ሊያካሂዱ በፍጹም አይችሉም።  እንዲሁም ባህልን ከስካሽና ስነ-ልቦናን አድክሞ አንድን ህዝብ አቅመ-ቢስ እንዲሆን ከሚያደርገው ከአጠቃላዩ የህወሃት አሰራር ለመላቀቅ ያልቻሉት ከወጣትነታቸው ጀምረው በተበላሸ አስተሳሰብ መንፈሳቸው በመታነጹ ነው። ለዚህ ደግሞ የወያኔ አገዛዝ በአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝምና ዓለም አቀፋዊ በሚባሉ ተቋማት ተገዶ ተግባራዊ ያደረገው የኢኮኖሚ ፖሊሲ ወሳኝ ሚናን እንደተጨዋተ ማረጋገጥ ይቻላል።  የኒዎ-ሊበራልን የኢኮኖሚ ፖሊሲ ተግባራዊ ማድረጉ፣ ከውጭው ዓለም ዕርዳታ ማግኘቱ፣ በዓለም አቀፍ የጦርነት ስልት ስትራቴጂ ውስጥ በመግባት በአካባቢው ጦርነት በማካሄድና፣ ወደ ውስጥ ደግሞ ግድያን፣  በተለያዩ የማሰቃያ ዘዴዎች ህዝባችንን ማሰቃየትና ወጣቱ እንዲሰደድ ማድረግ፣ ጎሳንና ሃይማኖትን አሳቦ የእርስ በርስ ጦርነት እንዲነሳ ማድረግና፣ አገራችንን ዘለዓለማዊ የጦር አውድማ ማድረግ፣ ህዝባችንም የራሱን ታሪክ እንዳይሰራ መሰናክል መፍጠር፣ እነዚህ ሁሉ ከአሜሪካን ኢምፔርያሊዝምና ግብረአበሮቹ የውዝግብና የማተረማመስ፣ የህዝብን ቁጥር ከመቀነስ ስትራቴጂና ፓለቲካ ጋር በጥብቅ የተያያዙ ናቸው። ስለሆነም ወያኔ ወደ ዘራፊነት የተቀየረውና ሀብትን በከፍተኛ ደረጃ ማውደም የቻለው በግሎባል ካፒታሊዝምና በተቋማቱ በመደገፉ ብቻ ነው። የአቢይ አህመድ አገዛዝም ከጆርጅ ሶሮን ከመሳሰለው በሄጅ ፈንድ ከደለበው ጋር የጠበቀ ግኑኝነት ሊኖረው የቻለው የአሜሪካንን የነጭ ኦሊጋርኪ ጥቅም ስለሚያስጠብቅ ብቻ ነው። ይህንን የማይቀበል የፖለቲካ ታጋይ ነኝ ባይ ኢትዮጵያዊ ስለ ዲሞክራሲና ነፃነት፣ እንዲሁም ስለ ሁለ-ገብ ዕድገት በፍጹም ሊያወራ አይችልም። በሳይንስና በቴክኖሎጂ ላይ የተመሰረተ ጠንካራ ኢኮኖሚ ለመገንባትና የተከበረች አገርም ለመፍጠር አይችልም። እንደዚህ ዐይነቱ ሰው ደግሞ ሰው ነኝ ሊል አይችልም። ስለሆነም ኢትዮጵያዊም ነኝ እያለ ሊዘባነን በፍጹም አይችልም።

 

የኒዎ-ሊበራል ኢኮኖሚ ፖሊሲ ተግባራዊነት ለወያኔ አገዛዝ

ሀብትን መዝረፍ አመቺ ሁኔታን ፈጥሮለታል !

ወደ ፖሊሲው ተግባራዊነትና አሉታዊ ተጽዕኖ ከመግባቴ በፊት ኒዎ-ሊበራሊዝም ማለት ምን ማለት እንደሆነ መረዳቱ በጣም አስፈላጊ ነው። ጽንሰ-ሃሳቡንና ውጤቱን በሚመለከት በሁላችንም ዘንድ የመረዳት ችግር አለ። አብዛኛዎቻችን የአንድን ጽንሰ-ሃሳብ ወይም ፖሊሲ አፀናነስ፣ ማደግና ወደ ተግባር ተመንዝሮ ዓለም አቀፋዊ ባህርይ እንዴት ለመያዝ እንደቻለና፣ የጽንሰ-ሃሳቡን ይዘት ለመመርመርና ከህብረተሰብ ዕድገት ጋር ለማገናኘት ገቱ ስለሌለን ዝም ብለን እንናገራለን። አንዳንድ የፖለቲካ ታጋይ ነን የሚሉ ድርጅቶች ደግሞ በአገራችን ምድር ምን ዐይነት የኢኮኖሚ ፖሊሲ ተግባራዊ እንደተደረገ ሳይመረምሩ የፖለቲካውን ሜዳ በመያዝ የባሰ ውዥንብር ይነዛሉ። አንድን አገር ለመገንባትና እንደማህበረሰብ በፀና መሰረት ላይ ለማቆም ደግሞ የግዴታ  አንድን ጽንሰ-ሃሳብ በሚመለከት የአስተሳሰብ ጥራት መኖር አለበት። አንድ አገር እንደ ህብረተሰብ እንዲገነባ ከተፈለገ ግብዝነትና ፉከራ ወይም ቀረርቶ ቦታ የላቸውም። ለአንድ አገር ግንባታ ዋናው ቁልፍ የሆንኑ ነገሮች ሳይንሳዊ አስተሳሰብና አርቆ-አሳቢነት ብቻ ናቸው  በመሆኑም የያንዳንዱን የፖለቲካ ድርጅት ወይም አክቲቪስት አቋምና ሀቀኝነት ለማወቅ እንደዚሁ የሃሳብ ጥራት ያስፈልጋል። አንድ አገር ሊገነባና ህዝቡም የተሟላ ነፃነት ማግኘት የሚችለው በሳይንስና በፍልስፍና እየተመራ ንቃተ-ህሊናውን ሲያዳብርና ማንነቱን ሲያውቅ ብቻ ነው። በቁጥር እየጨመረ ለሚሄድ ህዝብ ሰፋ ያለ የስራ መስክ ለመክፈት ትናንሽና ማዕከለኛ ኢንዱስትሪዎች ያስፈልጋሉ። እነዚህ ደግሞ በሳይንስና በቴክኖሎጂ መደገፍ አለባቸው። ከተማዎችን በተሟላ መልክ ለመገንባት እንደዚሁ ሳይንስና ቴክኖሎጂ በጣም አስፈላጊ ናችው።  ለዚህ ሁሉ ደግሞ የተፈጥሮ ሳይንስን ውስጣዊ ምስጢርና የፖለቲካ ኢኮኖሚ ህግን መረዳት በጣም አስፈላጊ ነው። ካለበለዚያ ኢትዮጵያ ኢትዮጵያ እያሉ መጮህ፣ ወይንም የጊዜው ጥያቄ ኢትዮጵያዊነት ነው እያሉ መናገር ትርጉም የላቸውም። ለሚራብና ለሚጠማ፣ እንዲሁም ነፃነቱ በተቀነባበረ መልክ በውጭና በውጭ ኃይሎች ለተረገጠበት ህዝብ፣  የኢኮኖሚ ፖሊሲ የሚባለውን ነገር የዓለም አቀፍ ኮሙኒቲው በሚባለው የሚወጣና የሚደነገግ ከሆነ ስለኢትዮጵያዊነት ማውራት ምንም ትርጉም አይሰጥም።

በመሰረቱ ኒዎ-ሊበራሊዝም የሚባለው ጽንሰ-ሃሳብ እ.አ በ 1938 ዓ.ም ለመጀመሪያ ጊዜ የተፈጠረ ሲሆን፣ ዋናው መሰረቱም የተጣለው በ1880 ዓ.ም ገደማ ነው። ጽንሰ-ሃሳቡን ባፈለቁት ምሁራን አስተሳሰብና ዕምነት መንግስት በኢኮኖሚ ፖሊሲ አማካይነት የገበያውን ተዋንያን ማደናቀፍ የለበትም። ማንኛውም ኢኮኖሚያዊ ክንዋኔና አንድን ህብረተሰብ የሚመለከቱ ጉዳዮች በሙሉ በገበያ ህግ መሰረት መደንገግ አለባቸው። እያንዳንዱ ግለሰብ እንደ ህብረተሰብ አካል የሚታይ ሳይሆን የራሱን ጥቅም ለማሳደግ የሚሯሯጥ ነው። በዚህ ዐይነቱ ግለሰብአዊ ሩጫ የመጨረሻ መጨረሻ ሁሉም ተጠቃሚ ይሆናሉ ይለናል። በአንድ አገር ውስጥ የሚገኝን የተፈጥሮ ሀብት ቁጥጥር ጉዳይና መሬትንም ጨምሮ በኒዎ-ሊበራል የኢኮኖሚ ፖሊሲ አውጭዎች ዘንድ ሁሉም ነገር በገበያ ህግ የሚደነገግ ወይም እንደ ተሰጠ(as given)ተደርጎ ነው የሚታየው። የቤት ወይም የመኖሪያና እንዲሁም የህክምናና የትምህርት ጉዳይ በገበያ ህግ የሚወሰኑ ናቸው። በኒዎ-ሊበራል አስተሳሰብ አንድ አገር እንደ ገበያ መድረክ ስለሚታይ፣ ባህል፣ ግብረ-ገብነትና ስነ-ምግባር ቦታ የላቸውም። የሚያማምሩ ከተማዎችና ጋርደኖች፣ እንዲሁም የባህል መንደሮች በኒዎ-ሊበራል አስተሳሰብ  በግምት ውስጥ የሚገቡ አይደሉም። በመሆኑም ገንዘብ ያለው ብቻ ሁሉን ነገር የሚደነግግበት፣ አንድን ህብረተሰብ እሱ በመሰለው የሚያሽከረክርበት ነው። ደሀና አካለ-ስንኩላት እንዲሁም የደከሙ ሽማግሌዎች  ቦታ የላቸውም። ይህም ማለት የፖሊሲው አውጭዎችና አራማጆች አስተሳሰባቸው ሶሻል ዳርዊኒዝም ወይም አረመኔያዊ አስተሳሰብን(Barbarian Ethos) ያዘለና የፋሺዝም መሰረት ነው። ይህ ዐይነቱ የኢኮኖሚ ፖሊሲ ነው በተለይም ባለፉት አርባ ዐመታት በዓለም አቀፍ ደረጃ እንደ ቫይረስ በመስፋፋት አገሮችን የሚያተራምሰውና ለዘራፊ መንግስታት መሰረት በመሆን አንዱ ሌላውን እየፈራ እንዲኖር የተደረገበት ሁኔታ ሊፈጠር የቻለው። በዚህ ዐይነት ህብረተሰብ ውስጥ የመንግስት መኪናዎች፣ ማለትም የሚሊታሪው፣ የፀጥታውና የፖሊሱ የጥቂት ሀብታሞችን ጥቅም ማስጠበቂያ በመሆን በህዝብ ላይ ጦርነት እንዲያካሂዱ ለማድረግ በቅተዋል። ስለሆነም በአንድ አገር ውስጥ የሚኖር ከዘጠና በመቶ በላይ የሚሆን ህዝብ እንደ እንግዳ ወይም እንደ አላስፈላጊና ትርፍ(Redundant) ነገር በመታየት በውጭ ኃይሎች በተቀነባበረና በተቀመጠ አገዛዝ ህልውናውን እንዲያጣ ለመደረግ በቅቷል ማለት ይቻላል። በማዕከለኛውና በላቲን አሜሪካ አገሮች ያለውን አደገኛ ሁኔታና የህዝብ ፍልሰት መመልከቱ በቂ ምሳሌ ነው። ከዚህ በመነሳት ነው በአገራችን ምድር ተግባራዊ የሆነውን የኢኮኖሚ ፖሊሲ መረዳት የሚቻለው።

የሚያሳዝነው ጉዳይ 27 ዓመታት ያህል በኢትዮጵያ ምድር ተግባራዊ በሆነው የኢኮኖሚ ፖሊሲ ላይ አንዳችም የፖለቲካ ታጋይ ነኝ የሚልም ሆነ የኢኮኖሚ ምሁር አመርቂ ጥናት ለማቅረብ አልቻለም። እንዲያውም በአብዛኛዎቹ ግንዛቤ የወያኔ አገዛዝ እስከዛሬ ድረስ ተግባራዊ ያደረገው የኢኮኖሚ ፖሊሲ የመንግስት ልማታዊ ፖሊሲና አብዮታዊ ዲሞክራሲ እንጂ ሌላ ነገር አይደለም  እያሉ  ነው ይነግሩን የነበረው። በአገራችን ምድር አፍጦ አግጦ ለታየው ቀውስና አገዛዙን እንዲወድቅ ያደረገው ይኸው በመንግስት የተደገፈ የኢኮኖሚ ፖሊሲ ተግባራዊ በመሆኑ ብቻ ነው ይሉናል። የኒዎ-ሊበራል የኢኮኖሚ ፖሊሲን በሚመለከት ከአስር ጊዜ በላይ በሳይንስና በተነፃፃሪ ትንተና(Comparative studies) ለማረጋገጥና ለማሳመን ቢሞከርም ታጋይ ነኝ ባዩና የኢኮኖሚ ተንታኝ ባዩ አሻፈረኝ በማለት አሁንም ድርቅ በማለት „ወያኔ ሲያራምድ የነበረው በመንግስት የተደገፈ ልማታዊ ፖሊሲ ነው“ እያለ ከሳይንስና ከተጨባጭ ሁኔታዎች ባሻገር ልባችንን ሲያደርቀው ከርሟል። ይህ ዐይነቱ ችኮነትና ፀረ-ሳይንስ አመለካከት ትርጉሙ ሊገባኝ በፍጹም አይችልም።

ያም ሆነ ይህ በካፒታሊስት አገሮች የህብረተሰብ ዕድገት ታሪክ ውስጥ የኒዎ-ሊበራል የኢኮኖሚ ፖሊሲ እንደ ዕድገት መመሪያ ተግባራዊ የሆነበት ጊዜ የለም። ከ14ኛው ክፍለ-ዘመን ጀምሮ ካፒታሊዝም ስር መስደድና መቆናጠጥ እስከጀመረበት እስከ 20ኛው ክፍለ-ዘመን ድረስ ተግባራዊ የሆነውን የኢኮኖሚ ፖሊሲ ስንመለከት በመንግስት የተደገፈ ፖሊሲ መሆኑን ማረጋገጥ ይቻላል። በተለያየ ዘመናት ወይም ኤፖኮች እንደ ኃይል አሰላለፍ የተለያዩ የአውሮፓ መንግስታት ጣልቃ-ገብ ፖሊሲዎችን በማካሄድ ለካፒታሊዝም ዕድገት፣ ማበጥና ዓለም አቀፋዊ ባህርይን ለመያዝ ዕምርታን ሰጥተውታል። ይህንን በሚመለከት በሺህ የሚቆጠሩ የኢምፔሪካልና የቲዎሪ ጥናቶች አሉ። የኒዎ-ሊበራሊዝምን ፖሊሲ በሚመለከት አሁን በቅርቡ የወጡ ሁለት መጽሀፎችና የቀድሞው የግሪክ የገንዘብ ሚኒስተር የነበሩት ፕሮፌሰር ፋሮፋኪስ እንደሚያረጋግጡት ኒዎ-ሊበራሊዝም የኢኮኖሚ ፖሊሲ እንዳልሆነና አገርንም ለመገንባት የሚያመች እንዳይደለ ነው። እንደ ሃይማኖት ከመያዙና ከመሰበኩ በስተቀር ሳይንስ እንዳልሆነ ይነግሩናል። ስለሆነም በአውሮፓው የህብረተሰብ ታሪክ ውስጥ ካፒታሊዝም ሊያድግ የቻለው የተለያዩ ዕውቀቶች፣ ማለትም ፍልስፍና፣ የተፈጥሮ ሳይንስና ቴክኖሎጂ፣ የሶስይሎጂና የስነ-ልቦና ዕውቀቶች አንድ ላይ በመጣመራቸውና አንድ ህብረተሰብም እንደ ሁለንታዊ ነገርና እርስ በእርሱ እንደተያያዘ በመታየቱና ግንዛቤ ውስጥ በመግባቱ ነው። አልፎ አልፎ ካፒታሊዝም ፈሩን ሲለቅና ህብረተሰብአዊ ኖርሞች ወደ መላላት ሲያመሩ፣ በተለይም የማህበራዊ ጥያቄዎችና(The Social Question)ባህላዊ ጉዳዮች አትኩሮ እንዲሰጣቸው ከፍተኛና የማያቋርጥ ትግል ይደረግ ነበር። በዚህ መልክ በአውሮፓ ምድር ውስጥ ምሁራዊ ዕድገት፣ በጥልቀትና በሰፊው ማሰብ፣ እንዲሁም አንድ ህብረተሰብ ተከታታይነት እንዲኖረው የማያቋርጥ ትግል ማድረግ እንደባህል የተወሰዱ ናቸው። በሌላ አነጋገር፣ አንድ ህብረተሰብ ወደ ገበያነትና መገባያያነት ብቻ ተቀንሶ መታየት እንደሌለበት በተገለጸላቸው የአውሮፓ ምሁራን ዘንድ ከፍተኛ ግንዛቤ ነበር። ይህ ዐይነቱ ግልጽና ፍልስፍናዊ አስተሳሰብ ግን በኒዎ-ሊበራሊዝም አይሎ መውጣትና በየተቋማቱ ውስጥ በመሰግሰጉና ፓርቲዎችንም በቁጥጥሩ ስር በማድረጉ ካፒታሊዝም ፈሩን ለቆ በመውጣት ብዙ  አገሮችን በማተራመስ ላይ ይገኛል። በተለይም የፋይናንስ ካፒታል የበላይነትን መቀዳጀት ሁሉንም የተፈጥሮ ሀብቶችና ሰውንም ጨምሮ ወደ ተራ ሸቀጣ ሸቀጥነት በመለወጡ የኑሮ ትርጉም ሊበላሽ ችሏል። በዓለም አቀፍ ደረጃ ጦርነቶች መስፋፋትና መንግስታት ህግን እየጣሱ የሌላውን አገር ህዝብ ማፈናቀልና መበታተን፣ ሌላውን ደግሞ አመጸኛ እንዲሆን ማድረግ ከግሎባል ካፒታሊዝም ጋር በጥብቅ የተያያዘ ነው። ይህ ግልጽ ሲሆን ብቻ ነው በአገራችን ምድር ተግባራዊ የሆነውን የኢኮኖሚ ፖሊሲና ውጤቱን መረዳት የሚቻለው።

ለማንኛውም ወያኔ ስልጣን በያዘ በዓመቱ ተግባራዊ ማድረግ የጀመረው የኒዎ-ሊበራልን የኢኮኖሚ ፖሊሲ ነው። በፖሊሲው መሰረትም፣ 1ኛ) የኢትዮጵያን ብር ከዶላር ጋር ሲወዳደር ዝቅ እንዲል ማድረግ(Devaluation)፣ 2ኛ) በመንግስት ቁጥጥር ስር የነበሩትን ወይም የህዝብ ሀብት የሆኑትን ፋብሪካዎችና የንግድ መደብሮችን በሺያጭ ወደ ግል ይዞታ(Privatization) ማዘዋወር፣ 3ኛ) የውጭውን ንግድ ልቅ ወይም ሊበራላይዝ ማድረግ፣ 4ኛ) የመንግስት በጀት ድጎማ በሚደረግላቸው ነግሮች ላይ፣ ምግብ፣ ትምህርትቤትና ጤንነት የመሳሰሉት ላይ በጀቱን መቀነስ፣ 5ኛ) የውስጡን ገበያ በገበያ ህግ  (Demand and Supply)እንዲተዳደር ማድረግ ናቸው የፖሊሲው ይዘቶች። ይህንን ዐይነቱን ፖሊሲ ዴሬጉሌሽን(Deregulation) ብለው ይጠሩታል። በሌላ አነጋገር፣ ኢኮኖሚው እንዳለ ከመንግስት ማነቆ መላቀቅና በገበያ ህግ መሰረት መተዳደር አለበት። ይህ ሲሆን ብቻ ኢኮኖሚው ያድጋል፤ የስራ መስክም ይከፈታል፤ ሰራተኛውም ገቢ ስለሚያገኝ በመግዛት ኃይሉ ለኢኮኖሚው ዕድገት ዕምርታን ይሰጠዋል። በዚያውም የኢትዮጵያ ህዝብ እንዳለ ይፈነጥዛል፣ ወይም በደስታ ዓለም ውስጥ ይኖራል ይሉናል።

የዚህን ፖሊሲ ውጤት ስንመለከት፣ በተለይም የመንግስት ሀብትን ወደ ግል በማዘዋወሩ ላይ ተጠቃሚ መሆን የቻሉት የወያኔ ሰዎችና ከሱ ጋር በጥቅም የተቆላለፉና ትልቁ ኩባንያው ኢፈርት የሚባለው ነበሩ። ስለሆነም የወያኔ ሰዎች ከባንክ በቀጥታ ብድር በማግኘት ካለምንም ነፃ ውድድር የመንግስትን ሀብት በመቀራመትና ስትራቴጂ የኢኮኖሚ ንዑስ-መስኮችን፣ እንደ እጣን፣ ቡናና ሻይ እንዲሁም ሰሊጥና ኑግን የመሳሰሉትን በመቆጣጠር በአጭር ጊዜ ውስጥ የናጠጡ ሀብታሞች ሊሆኑ በቅተዋል። ከዚያም አልፈው የወርቅና ሌሎች በጣም ጠቃሚ የሆኑ ማዕድኖችን በመቆጣጠርና ቆፍሮ እንዲወጣ በማድረግ በከፍተኛ ደረጃ የሀብት ዘረፋ ማካሄድ ችለው ነበር። ከዚህ በተጨማሪ መሬትን በከተማም ሆነ በገጠር ውስጥ በመቀራመትና ህዝቡን በማፈናቀል የኢትዮጵያን ህዝብ ዕድል በእጃቸው ስር ማድረጋቸው ብቻ ሳይሆን፣ ኢትዮጵያን እንደፈለጋቸው ማሽከርከር ችለው ነበር። ይህ በራሱ ልዩ የሆነና በህይወታቸው ያላለሙትን የኢኮኖሚና የማህበራዊ ስታተስ እንዲያገኙና የተንደላቀቀ ኑሮ እንዲኖሩ አስችሏቸው ነበር። ትላልቅ ቪላ ቤቶችንና መዝናኛ ቦታዎችን በመገንባት ከሌላው የተሻሉ እንደሆኑ ለማሳየት ሞክረዋል። ይሁንና ግን በምሁርም ሆነ በባህል ደረጃ የአስተሳሰብ ለውጥ ማድረግ እንዳልቻሉ፣ እንዲያውም እየናጠጡ በመጡ ቁጥር ጭንቅላታቸው እየታወረና የነገሮችን ሂደት ለመገንዘብ ያልቻሉበት ሁኔታ እንደተፈጠረ ከድርጊታቸው መገንዘብ እንችላለን። በዚህ ዐይነቱ ዐይን ያወጣና ህገ-መንግስቱን፣ የተፈጥሮንና የህብረተሰብን ህግ በሚፃረር የሀብት ዝርፊያ ውስጥ እንደነ አላሙዲን የመሳሰሉት በስለላ ድርጅት ውስጥ የታቀፉ ቱጃሮች በመካተት፣ በአንድ በኩል በሀብት ዘረፋነት ሲሰማሩ፣ በሌላ ወገን ደግሞ ሰፊውን ህዝብ ወደ ድህነትና አቅመ-ቢስነት ገፍትረውት እንደነበር ይታወቃል። በዚያው መጠንም የተወሰነውን የህብረተሰብ ክፍል በማባለግ የባህል ውድመት እንዲፈጠር ለማድረግ በቅተዋል።  በዚህ መልክ ለወያኔ ያደሩ ግለሰቦችን በሀብት ዘረፋ ውስጥ እንዲካተቱ በማድረግ አገዛዙ የተወሰነ ደጋፊ ኃይል(Social Base) ለማፍራትና ጭቆናውንና ዘረፋውን ለማስፋፋትና ጥልቀት እንዲያገኝ አመቺ ሁኔታ ፈጥሮለታል። ይህም ማለት በዚህ ዐይነቱ የዘረፋና የአገር አውዳሚነት ሂደት ውስጥ ከተለያዩ ብሄረሰብ የተውጣጡ ግለሰቦችም እንደተካተቱበትና፣ ከውጭ የጥፋት ኃይሎች ጋር በመመሰጣጠርና በመተባበር የአገራችን ሀብት እንዲዘረፍና ህዝባችንም እንዲደኸይ ለመደረግ እንደበቁ ማረጋገጥ ይቻላል።

ይህ ዐይነቱ የኒዎ-ሊበራል የኢኮኖሚ ፖሊሲ የተቋም መሰተካከል ዕቅድ(Structural Adjustment Programms) በመባል ሲታወቅ፣ በፕሬዚደንት ሬገንና በወይዘሮ ቴቸር አገዛዝ ዘመን በ1980ዎቹ ዓመታት መጀመሪያ ላይ በታወቀው የኒዎ-ሊበራል ኢኮኖሚክስ አራማጅ በሚልተን ፍሪድማንና ጓደኞቹ የረቀቀና የሶስተኛው ዓለም አገሮች ተግባራዊ እንዲያደርጉት የተደነገገ ነው። በአርቃቂዎቹና ኃላፊነትን በተሰጣቸው መሪዎች ዕምነትና ፍላጎት ጠቅላላውን የዓለም ህዝብ በገበያ ኢኮኖሚ ፖሊሲ ስር በማካተት የአሜሪካንን የበላይነት ማስፈን ነው። ስለሆነም በየአገሮች ውስጥ የተወሰነው የህብረተሰብ ክፍልና አገዛዞች በዚህ ዐይነቱ ዕቅድ ስር በመካተት፣ በአንድ በኩል ወደ ውስጥ የሀብት ሽግሽግና ዘረፋ በማካሄድ ያልተስተካከለ ዕድገት(Unequal Development) ተግባራዊ ማድረግ ሲሆን፣ ወደ ውጭ ደግሞ ሀብት የሚሸሽበትን ዘዴ ማመቻቸት ነው። ብድርና የተዛባ የውጭ ንግድ ዋናው የሀብት ማዘዋወሪያ መሳሪያዎች ናቸው። በዚህ መልክ ፖሊሲው ከጋና እስከናይጄሪያና ዚምባብዌ ድረስ፣ እንዲሁም በራሺያ ከ1989 ዓ.ም በኋላ ተግባራዊ በማድረግ ለኦሊጋርኪዎች መነሳትና የሀብት መዝረፍ ምክንያት ለመሆን በቅቷል። በእነ ዓለም ባንክና በዓለም የገንዘብ ድርጅት ዕምነት አንድ የኢኮኖሚ ፖሊሲ ከጠቅላላው ህዝብና ከየአገሩ የማቴሪያል ሁኔታ በመነሳት መነደፍ ያለበት ሳይሆን፣ የተወሰነውን የህብረተሰብ ክፍል ብቻ መነሻ በማድረግና በዓለም አቀፍ አገዛዝ ሂራርኪ ውስጥ በማስገባት ነው መነደፍና መዋቀር ያለበት። ስለሆነም በየአገሩ ውስጥ ያለ ሰፊ ህዝብ እንደትርፍና(Redundant)
https://amharic-zehabesha.com/archives/181975

No comments:

Post a Comment

https://youtu.be/VUfa5eupQTc?si=Zm73w18dFB27xlqD       https://youtu.be/LcFmz2Xq5MY?si=7uP6VZsd2ksEulUf   https://youtu.be/7dUVmj8go7s?si=Px...