Friday, March 24, 2023

ጦርነት ማዳፈን ሠላም ማስፈን እንዴት ይሆናል ?  
#image_title

ኢትዮጵያ ከ1983 ዓ.ም. ጀምሮ ግንቦት 20 ይዞት የመጣዉ የማይቋጭ መከራ  ለኢህአዴግ የሥልጣን መከዳ በመሆን በህዝብ እና በአገር ላይ ለደረሰዉ ፖለቲካ አመጣሽ የሰለሳ ዓመታት  ጥፋት ተጠያቂ እንዳይሆንም መከላከያ ሆኖታል ፡፡

ላለፉት ሶስት አሰርተ ዓመታት ከፍተኛ የአገር ክህደት ፣ የዜጎች በማንታቸዉ እና ኢትዮጵያዊ በመሆናቸዉ ፣ በዕምነት እና አመለካከት የአገር ጉዳይ የህልዉና ጉዳይ መሆኑን በመረዳታቸዉ  ፍጂት፣ ዕልቂት ፣ ዕንግልት፣ ስደት ፣ መፈናቀል ፣ ዉርደት እና ባርነት አስተናግደዋል ፡፡

ኢትዮጵያም ሆነ ኢትዮጵያዉያን ስለ አገር አንድነት እና ሉዓላዊነት ፤ ስለህዝቦች አንድነት እና ደህንነት ህዝባዊ እና ብሄራዊ  ቅንነት   እና ቁርጠኝነት ያለዉ  የፖለቲካ ተቋም መሪ እና ዘዋሪ ባለማግኘት እና ባለመለየት መሪ አልባ በመሆን አሁን ከደረስነበት ተደርሷል፡፡

ኢህአዴግ ከሽግግር ዘመን ጅምር አስካዘሬ መደመር ከህዝብ እና ከብሄራዊ ፍላጎት እና ጥቀም በተቃራኒ በመሄድ የቁራ ፖለቲካ ሲያራምድ ከራሱ ዉጭ የሚስተጋባዉን  መከራ እና ዋይታ  እንደ ደስታ እና ርካታ ሲወስደዉ ማየት ዛሬ ላይ አዲስ ሊሆን ባልተገባ ነበር ፡፡

የእኛ አገር ፖለቲከኞች  ስለ ህዝብ እና አገር እየተናገሩ  ለዘመናት ሲምሉ ፤ሲገዘቱ  ግን የህዝብ መከራ ሰቆቃ ከማይሰማበት የቁራ ዛፍ ተጠልለዉ ኢትዮጵያዊነት እና ብሄራዊ አንድነት ይመጣል ብለዉ ተስፋ ሲያደርጉ ማየት በእጂጉ የሚያሳዝነዉ እና ከኢትዮጵያ ግልፅ ጠላቶች ይልቅ ጠላቶች ወይም ተባባሪዎች ሆነዋል ፡፡

በኢህአዴግ ህገ መንግስት እና በኢህአዴግ  የጥላቻ እና ከፋፋይ የፖለቲካ  መስመር   በኢትዮጵያ ሰማይ ስር የሆኑት እና የተደረጉትን በአገር እና በህዝብ ላይ የተፈፀሙ ደባዎች  አለማስታወስ  እና ከዚህ አለመመለስ እየታየ በጥፋት ላይ ጥፋት በሚደራረብባት አገር መናጆ የሆኑ ፖለቲካ ድርጂቶች ኢትዮጵያን ከሚገዘግዟት በላይ ተጠያቂዎች ናቸዉ ፡፡

ለዓመታት በህገ  ኢህአዴግ  ሽፋን በክልል አደረጃጀት እና በህዝብ መለያየት ለደረሱ ሠባዊ እና ቁሳዊ ጥፋቶች ብሄራዊ ጥፋት እና ክህደት መሆኑን እያወቁ  በዝምታም ሆነ በይሁንታ ያለፉ ህዝብን እንወክላለን የሚሉ ፖለቲከኞች ከህዝብ እና ከአገር ይልቅ ተመሳስሎ መኖርን መምረጣቸዉ ከህዝብ መኃል ሆነዉ የቁራ ጩኸት ቢያሰሙ ከቁራ ዛፍ ስር መሸጎጣቸዉ ከታሪክ እና ከተዉልድ ተጠያቂነት አያድናቸዉም ፡፡

ሁላችንም እንደምናዉቀዉ ህዝብ በሁሉም ነገር ከፊት ሆኖ መሪ ነን የሚሉት ከኋላ ሆነዉ  ለአገር እና ለነፃነት የተከፈሉ ዋጋዎች እጂግ ብዙ ናቸዉ ፡፡ ለወትሮዉ ዞትር በአገር እና በህዝብ ጉዳይ ኢትዮጵያዉያን መሪዎች ከህዝብ እና ከአገር በፊት ራሳቸዉን  በኢትዮጵያዊነት ልክ ከጠላት ፊት ቆመዋል ፡፡ ለዚህም የዓደዋዉን ፣ የካራ ማራዉን ጦርነት እና የጦር ዉሎ ማስታወስ በቂ ነዉ ፡፡ ሚኒሊክ በዓደዋ ፤ መንግስቱ በካራ ማራ…… በጦርነት  ግንባር ተገኝተዋል ፡፡ ወደ እኛ ዘመን ስንመጣ በኢትዮጵ ፤ኤርትራ የኢትዮጵያ ህዝብ እናት አገር ወይም ሞት ብሎ ያለ መሪ ወደ ጦር አዉድ ተምሞ  በተከፈለዉ የህይወት ፣ደም ፣ አካል …ዋጋ ዉጤቱ ምን እንደሆነ  የቅርብ ዘመናት መሪር ትዝታ ነዉ ፡፡

ይህ አልበቃ ብሎ  ትህነግ /ኢህአዴግ ጥቅምት 24/2013 ዓ.ም.  ከታዘልኩ አልወርድም በሚል አባዜ ወደ ነፃ አዉጭነት ራሱን መልሶ የፈረደባቸዉ ኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያዊነት ፤ዓማራነት ተዘመተባቸዉ ፡፡ ይህም በመከላከያዉ ለይቶ ማጥቃት ፣ ቀጥሎ በጎንደር ፣በወሎ ፣በሸዋ……ወረራራ በማድረግ ህዝቡን በማወረድ ፣በማሳደድ እና  በማስወገድ የግዛት ማስፋፋት እና  አገረ ትግራይ መገንባት በሚል ዕብሪት በታሪክ የማይታወቅ ዘግናኝ ዕልቂት ፣ ሞት ፣ ምዝበራ እና የሠባዊ መብት ወንጀል በኢትዮጵያ ህዝብ በሆነዉ ዓማራ እና አፋር ላይ ተፈፅሟል ፡፡

በዚህ ራስን የመከለካከል እና ነፃ  የማዉጣት የህልዉና ተጋድሎ  ሁሉም ኢትዮጵያዊያዉያን ይነስም ይብዛ ፤ በተለይም ዓማራ እና አፋር የመከራዉ እና የጦርነቱ ዒላማ እና  ሞት የተፈረደበት ህዝብ  ማቄን ጨርቄን ሳይል አስካፍንጫዉ የታጠቀ ጠላት ጋር በፉፁም ብሄራዊ እና ህዝባዊ ወኔ በመተናነቅ  ተደጋጋሚ እና ዕልህ አስጨራሽ  ትግል ኢትዮጵያ ፣ኢትዮጵያዉያን እና የኢትዮጵያ የቁርጥ ቀን ልጆች አገር እና ህዝብ ከክህደት አዋላጆች እና አራማጆች ተከላክለዋል ፡፡

ኢትዮጵያን ያዳነ የኢትዮጵያ ጠላቶችም አድኗል ፡፡ በመዳናቸዉም እንደገና ኢትዮጵያዉያን እና ኢትዮጵያን ለማቁሰል  ሲንደረደሩ ማየት “ባሪያን ነፃ ያወጣ ጌታዉን ነፃ ያወጣል ” እንዲሉ የዓማራ ህዝብ እና የአብራኩ ክፋዮች  የክልሉ መደበኛ የፀጥታ ኃይል ፤ ፋኖ  እና ሁሉም በሚባል“ የትናንት  እና ከድል ማግስት ጠላት የሆኑትንም ” ለዛሬ ማድረሱ ጀግና የባሪያን ጌታ ብቻ ሳይሆን ጠላትንም ታድጓል፡፡

ዛሬ ጦርነት አዳፍኖ ሠላም ሠላም ሲባል ለሠላም ፤ ለአገር አንድነት እና ለህዝብ ሉዓላዊነት የተከፈለዉን ዋጋ ፤ ጀግኖችን እና የጠፋዉን ጥፋት በማደባበስ ሳይሆን በግልፅ በመንቀስ እና በማወደስ  ለሁሉም ዕዉቅና እና ተጠያቂነትን ማስፈን ግድ ይሆናል ፡፡

ከጦርነት መሸሽ ጦርነት አያስቀርም ፡፡ ይህ ለአገር እና ህዝብ ዘላቂ መፍትሄ ከሚኖረዉ ይልቅ አጠያያቂ ጉዳይ ይዞ ይቀጥላል ለምን ካሉ የተጎዳ ባልተካሰበት ፤ የጎዳ ባልተጠየቀበት ይድረስ ይድረስ ከወንጀል እና ከታሪክ ተጠያቂነት አያድንም ፡፡

የኢትዮጵያ ህዝብ በተለይም የዓማራ ህዝብ ለአለፉት ሶስት አሰርተ ዓመታት አገር አልባ እና ባይተዋር በአገሩ ሲሆን እና ለደረሰበት ዕልቂት ቀድሞ የነበረዉን ብሄራዊ እና ህዝባዊ የአገር መከላከያ በማፍረስ ኢህአዴግ አርሶ አደሩ በነፍስ ወከፍ  ከጉርሱ እና ልብሱ ቀንሶ የገዛዉን መሳሪያ ቀምቶ ባዶ እጁን ቁም ቅምጥ ሲነሳ መኖሩ ተርስቶ ዳግም በዘመናዊ ጦር መሳሪያ ለሠላሳ ዓመት በተደረገ ኢትዮጵያን ለማፍረስ እና ዓማራን ለማሳነስ ዳግም ቀጥታ ወረራ እና ምዝበራ ማድረግ እና ይህን ተከትሎ በተደረገ የህዝብ የመከላከል ተፈጥሯዊ መብት የዓማራ ህዝብ ራሱን እና አገሩን የመከላከል ሠባዊ እና ኢትዮጵያዊ መበቱን ከማንም የሚጠብቅ መሆን የለበትም ፡፡

በአንድነት ክንድ እና በፅናት ህልዉናዉን ለማስቀጠል ባይዋደቅ ኖሮ ዛሬ አገርም ነጻነትም ጠፍቶ ጭራሽ ተንበርካኪ በሆን ነበር ፡፡

የዓማራ ህዝብ የኢትዮጵያን አንድነት እና ሉዓላዊነት ላይ ካለዉ እና ከሚኖረዉ ቁርጠኛ አቋም አኩያ የተረፈችዉን ኢትዮጵለማስቀጠልም ሆነ ኢትዮጵያዊነትን ለማረጋገጥ የኢትዮጵያ  ህዝብ በተለይም ዓማራ ከሞት ፣ ባርነት እና ስደት ቀንበር ለመላቀቅ ብቸኛዉ መንገድ ከምንጊዜዉም በላይ ለራሱ እና ለአገሩ ዘብ መቆም አለበት ፡፡ ምንጊዜም ለራስ እና ለአገር ዘብ መቆም የነፃነት ዋጋ ነዉ ፡፡

ኢትዮጵያን እና ኢትዮጵያዉያን መዳኛቸዉ ራሳቸዉ እና ረሳቸዉ ብቻ ናቸዉ ፡፡ የኢትዮጵያዉያን ችግራችን ጠላት እንደማይተኛ ሳናዉቅ ፤ የእኛ መዘናጋት እና ህብረት ማጣት ከምንም በላይ ሊያሳስበን ይገባል፡፡

ሠላም ሆነ ጦርነት ሠወች በሚሉት የሚኖር ሳይሆን  ፍትህ እና ዕኩልነት በጠፋበት ፤ የግል እና የቡድን ጥቅም እና ፍላጎት በበዛበት ፤ ሠርቶ መኖር በሠዎች በጎ ፈቃድ በሚሆንበት ፤ በሀይወት የመኖር እና ዛሬ ዓለም የሰዉ ልጆች መንደር በሚባልበት በአገር የዜግነት ክብር እና መብት መጥፋት፤ ለአገራቸዉ እና ለራሳቸዉ ህዝብ ህልዉና ልዕልና ዋጋ የከፈሉበት ሊያሸልም ሲገባ እስር እና ዕንግልት………. ፤ ለህዝብ እና ለአገር ቅድሚያ እና ክብር አለመስጠት ከዚያ ላይ ለግል እና ቡድን ጥቅም መሯሯጥ በሚታይባት ምድር ስለ ሠላም ዋጋ ማነብነብ  ከልብ ይሆናል ብሎ ማሰብ የጦርነት ምንነት ማሳነስ ነዉ ፡፡ ርኃብ በርኃብ ፤ ስደት በስደት፣ ሞትበሞት….. “ደም በደም ለማንጻት ” እንደመሞከር ነዉ ፡፡

የጥላቻ መንፈስ አርግዞ ኢትዮጵያን እና ኢትዮጵያዊነትን በማሳነስ እና በማኮሰስ የሚደረገዉ ጥላቻ ወለድ ዘመቻ መነሻ እና መዳረሻ የሆነዉ ኅገ-ኢህአዴግ ባለበት ስለ ጦርነት እና ሠላም የሚወራዉ በቁራ ፖለቲካ ጥላ ስር ብቻ ነዉ ፡፡ ይህም “ቁራ ከራሱ ድምፅ ዉጭ የሚጥመዉ የለም ”እንዲባል ሠላምም ፤ጦርነትም የሚሉት ከመንደራቸዉ ዉጭ መንደር የማይታቸዉ ቀንድ አዉጦች ብቻ ናቸዉ ፡፡

በአገራችን በአሁኑ ጊዜ ሲደማመር የደረሰዉ ፈርጀ ብዙ የሠላም እና የመኖር ችግር በተለምዶ ጦርነት ከሚባለዉ በላይ ጦርነት መሆኑን በመረዳት ዕዉነት እና ርትዕ እንዲኖር ከመስራት ዉጭ አማራጭ ጦርነት ማዳፈን ሠላም ማስፈን አይሆንም ፡፡ጦርነትን ማዳፈንም  ሆነ መሸሽ ጦርነትን አያስቀርም ፤ ሠላምም አያስገኝም ፡፡

“የአገር እና ህዝብ ብቸኛ መዳኛ ዕዉነተኛ የቁርጥ ቀን ልጆች የህብረት ክንድ ብቻ ነዉ ፡፡”

አንድነት ኃይል ነዉ !

 

Allen Amber!
https://amharic-zehabesha.com/archives/180968

No comments:

Post a Comment

https://youtu.be/VUfa5eupQTc?si=Zm73w18dFB27xlqD       https://youtu.be/LcFmz2Xq5MY?si=7uP6VZsd2ksEulUf   https://youtu.be/7dUVmj8go7s?si=Px...