Sunday, February 26, 2023

ጻድቅ እያሰፈጀን እርጉም እያመለክን መኖር ቀጥለናል!

ጻድቅ እያሰፈጀን እርጉም እያመለክን መኖር ቀጥለናል!


መለኮት መላእክት ህሊና ሰውነት ታሪክ ምን ይለናል?

ጻድቅ እያስፈጀን እርጉም እያመለክን መኖር ቀጥለናል፡፡

 

ጭራቁን ዘንዶውን እባቡን ተኩላን ሙሴና እያሱ እያልን፣

በዜማ ያወደስን የአገር መሲህ እያልን ተእግራቸው ተደፍተን፣

የፍትህ ጠበቃን የእውነት ሐዋርያን ነቢዩ እስክንድርን አሳልፈን ሰጥተን፣

መኖር ስንቀጥል ምግብ ተመግበን መጠጡን ጨልጠን ከርስን ቁዝር አርገን፣

ጸጸትና ቁጭት ዞር ብሎ ታላዬን ተይሁዳ የባስን ከሀዲ ባንዳ ነን፡፡

 

ምቾትና ድሎት ደህና ሁኝ ብሎ ሚስቱን ልጁን ትቶ ቆርጦ የመነነ፣

እንደ ቅዱስ ጳውሎስ በሄደበት ሁሉ እስርና እንግልት እየተቀበለ፣

እውነትን ፍትህን ያለምንም እረፍት መስበክ የቀጠለ፣

በእኛ እድሜና ትውልድ እስክንድር ነጋ እንጅ ሌላማ የት አለ?

 

መነኩሴ ነኝ ባዩ ገዳም እየሸሸ አውሮጳ አሜሪካ ሲጋፋ እየዋለ፣

ፍትህን ፍለጋ ከአሜሪካ ወጥቶ ዋሻና ገዳም ውስጥ ሲጸልይ ያደረ፣

ከእስክንድር ነጋ ውጪ ማተብ ያሰረ ሰው ከቶ ተየት አለ?

 

ራስ ተዘቅዝቆ ሐዋርያው ሲታረድ ዝም እንዳለው መንጋ፣

ትናንትናም ዛሬም በእርጉማን ተይዞ ቅዱስ ሲንገላታ፣

ድምጥን እያጠፋን አፋችንን ለጉመን በጨጓራ ሞራ፣

እግዜር አስከፍተን አገርን፣ ታሪክን፣ ትውልድን አናጥፋ፡፡

 

ሕዝብ ሆይ ኮርኩር ህሊናህን ፈትሸው መርምረው፣

ዛሬ በእስክንድር ሥም በእርኩሶች ተይዞ ወህኒ ቤት ያደረው፣

የሰው ሥጋ አይደለም እውነትና ፍትህ ማተብ ጋር ሆነው ነው፡፡

 

ከጥፋት ውሀው ሰው ከሰዶም ገሞራም እጅጉን አንሰናል፣

አውሬም እንዳንባል የጅብ ያህል እንኳ ደመ ነፍስ ጎሎናል፣

ጻድቅ እያሰፈጀን እርጉም እያመለክን መኖር ቀጥለናል!

 

በላይነህ አባተ (abatebelai@yahoo.com)

የካቲት ሁለት ሺ አስራ አምስት ዓ.ም.

 

 

 

 

 

 
https://amharic-zehabesha.com/archives/180238

No comments:

Post a Comment

https://youtu.be/VUfa5eupQTc?si=Zm73w18dFB27xlqD       https://youtu.be/LcFmz2Xq5MY?si=7uP6VZsd2ksEulUf   https://youtu.be/7dUVmj8go7s?si=Px...