Tuesday, November 29, 2022

ስለኢምፔሪያሊዝም በአጠቃላይና፣ በተለይም ስለአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝምያለኝን የራሴን አቋም ግልጽ ለማድረግ ያህል! - ፈቃዱ በቀለ(ዶ/ር)
ፈቃዱ በቀለ(ዶ/ር)

        ህዳር 29፣ 2022

በአ.አ. በታህሳስ 15፣ 2022 ዓ.ም በወያኔና በአቢይ አገዛዝ መሀከል ስለተደረገው “የሰላም ድርድር” አስመልክቶ የአቶ አቡዱራህማን አህመድን ሰፊ ገለጻ በመመርኮዝ የጻፍኩትንና በዘሃበሻ ላይ ለንባብ ያቀረብኩትን ጽሁፍ አስመልክቶ ጽሁፉን ከአነበበ አንድ ምክር አዘል ነገር በትችት መልክ ቀርቧል።  ይኸውም ምክርና ገንቢ ትችት የአሜሪካንን ኢምፐሪያሊዝም አስመልክቶ ያቀርብኩት የእኔ የሆነ አመለካከት አላስፈላጊ እንደሆነ የሚጠቁም ነው። በተቺው ወንድሜ አስተያየት በአብዮቱ ወቅት የአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም ይውደም ብሎ የደርግ አገዛዝ ማስተጋባቱ የኋላ ኋላ አገዛዙን ለውድቀት አድርሶታል ይለናል።

በመሰረቱ የኢምፔሪያሊዝም ጥያቄ በደርግ አገዛዝዛና በመሪዎቹ የተነሳ ሳይሆን በተማሪው እንቅስቃሴ መሪዎችና ተከታዮቻቸው ነው። እንደሚታወቀው አፄ ኃይለስላሴ ከስደት ከተመለሱ በኋላ በጊዜው በነበረው የኃል አሰላለፍ ምክንያትና፣ የዓለምን ፖለቲካና አሉታዊ ተጽዕኖውን አስመልክቶ በአገራችን በነበረው ምሁራዊ ድክመትና ዝቅተኛ አስተሳሰብ የተነሳ አሜሪካንን እንደአጋርና እንደ ወዳጅ አገር በመውሰድ የአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም በተለይም በትምህርት ዘርፍ፣ በቴክኖክራሲውና በቢሮክራሲው መዋቅር ውስጥ፣ በሚሊታሪውና በጸጥታው ውስጥ ለብዙዎች ግልጽ ባልሆነ መንገድ የማይታይና የረቀቀ ተጽዕኖ እንደነበረው የሚታወቅ ጉዳይ ነው። ከዚህም በላይ ለአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም አዲስ አበባ ውስጥ በሁለት ጋሻ  በሚያክል መሬት ላይ ኤምባሲውን እንዲሰራ የተሰጠው “የወዳጅነት ልገሳና” ኤምባሲውም በዚያ መልክ መሰራቱ ይህንን በመጠቀም በአገዛዙና በኤሊቱ ላይ ከፍተኛ ተፅዕኖ ማሳደር ችሏል። የኤምባሲውም ዋናው ዓላማ ለራሱ የሚሆኑ በጥቅም የተገዙ ኢትዮጵያውያንን በመመልመል አጠቃላዩን የአገራችንን ዕድገት መቆጣጠርና፣ በዚያውም የሱን ጥቅም የሚጻረሩ የኢኮኖሚ ፖሊሲና የውጭ ፖለቲካ ግኑኝነት ተግባራዊ በሚሆኑበት ጊዜ ያለውን ልዩ ልዩ ህብረተሰብአዊ ቅራኔዎች፣ የሃይማኖትና የጎሳ ልዩነቶችን በመጠቅም ከውስጥ ብጥብጥ የሚፈጠርበትን መንገድ ማዘጋጀት ዋናው ስትራቴጂው ነው። በአፄ ኃይለስላሴ ዘመንም ሆነ በኋላ ብቅ ያሉትን አገዛዞች ፖለቲካ ስንመለከት ስትራቴጂያዊ በሆነ መልክ ማሰብ እንደማይችሉና የአገር ወዳድነት ስሜት እንዳልነበራቸውና እንደሌላቸው መገንዘብ የሚቻለው። ለዚህ ዋናው ምክንያት ደግሞ የበሰለና ብሄራዊ ስሜት ያለው በሁሉም አቅጣጫ ሊንቀሳቀስና ሊያስተምር የሚችል ምሁራዊ ኃይል ለመፈጠር ባለመቻሉ ነው።

በአጠቃላይ ሲታይ የአገራችንን የመንግስት አወቃቀር ስንመለከት፣ ከታች ወደላይ እየተኮተኮተ የመጣ መንግስታዊ አወቃቀርና አገዛዝ ለመፈጠር ባለመቻሉ በአፄ ኃይለስላሴ የሰላሳ ዓመታት የአገዛዝ ዘመን እዚህና እዚያ የሚብለጨለጩ ነገሮች ከመሰራታቸውና ውስጣዊ ኃይል የሌላቸው አንዳንድ ኢንዱስትሪዎች ከመቋቋማቸው በስተቀር አገራችንን እንደህብረተሰብ የሚያዋቅርና በራሱ የሚተማመንና የመሪነትን ቦታ ሊወስድ የሚችል የህብረተሰብ ክፍል ብቅ ሊል አልቻለም። መንግስታዊ መዋቅሩም ሁለ-ገብና አስተማማኝ የሆነ ሰፊውን ህዝባችንን ከድህነት የሚያላቅቀው የኢኮኖሚ ፖሊሲ ስላልነበረው ሰፋ ያለ ህዝባዊ ሀብት ለመፍጠር አልቻለም። የኢኮኖሚ ፖሊሲውም “እንደዚህ ብታደርጉ ይሻላል፣ ይህንን ፖሊሲ ተግባራዊ ብታደርጉ የኢኮኖሚ ዕድገት ለማምጣት ትችላላችሁ” የሚል በውጭ ኤክስፐርቶች ምክር የረቀቀና ተግባራዊ የሆነ በመሆኑ  በአጠቃላይ ሲታይ በአገሪቱ የተስተካከለና ሁለ-ገብ የሆነ የኢኮኖሚ ዕድገት በፍጽም ሊመጣ አልቻለም። በተለይም ከ1950ዎቹ መጀመሪያ ጀምሮ ተግባራዊ የሆነው የኢንዱስትሪ ፖለቲካ ለእርሻውና ለአገልግሎት መስኩ እንደዋና አንቀሳቃሽ ኃይል ሊሆን ባለመቻሉ የተነሳ በጊዜው እየጨመረ የመጣውን የህዝብ ቁጥርና ትምህርቱን ላገባደደ ወጣትና የስራ-መስክ ለሚፈልገው አስተማማኝ የኢኮኖሚ መሰረት መጣል አልተቻለም። በየክፈለ-ሀገራቱም የአስራሁለተኛን ክፍል እያገባደደ የሚወጣው  ቁጥሩ የማይናቅ ወጣት የስራ ቦታ ለመፈለግ ሲል የግዴታ ወደ አዲስ አበባ ይመጣ ነበር። ስለሆነም በጊዜው በውጭ ኤክስፐርቶች ግፊትና ምክር ተግባራዊ የሆነው የኢኮኖሚ ፖሊሲ አገራችንን ሁለ-ገብ ወደሆነና በሳይንስና በቴክኖሎጂ ላይ ወደተመሰረተ ሰፋ ወዳለ የኢኮኖሚ ግንባታ ለማሸጋገር ባለመቻሉ ህብረተስብአዊና ባህላዊ፣ እንዲሁም የስነ-ልቦና ቀውሶች ሊፈጠሩ ችለዋል። ህብረተሰቡም ሰፋ ባለ ኢኮኖሚያዊ መሰረትና አወቃቀር እንደ አንድ ኦርጋኒክ ኃይል ለመተሳሰር ባለመቻሉ፣ በአንድ በኩል ራሱን ከውጭው ዓለም ጋር ያስተሳሰረና ትዕዛዝ የሚቀበል፣ ራሱን እንደልዩ ፍጡር አድርጎ የሚቆጥር፣ በሌላ ወገን ደግሞ ግራ የተጋባና አቅጣጫው የጠፋበት ሰፋ ያለ የህብረተሰብ ክፍል በመኖሩ ምክንያት የተነሳ በአጠቃላይ ሲታይ ህብረተስባችን በደካማ መሰረት ላይ የቆመ ነበር ብሎ መናጋር ይቻላል። ባጭሩ አንድ አገርና ህብረተሰብ እንደ ሰውነታችን የማይታይ ከሆነ(Body Politics) በቀላሉ ሊፈረካከስ ይችላል። የጀርመን ፈላስፋዎች Body Politics ብለው የሚጠሩት ነገር አለ። እንደሚታወቀው ሰውነታችን ልዩ ልዩ ስራዎችን የሚያከናውኑ ልዩ ልዩ ኦርጋኖች ሲኖሩት፣ የእነዚህ መሰረቶች ደግሞ በብዙ ቢሊዮን የሚቆጠሩ ሴሎቻችን ናቸው። በደም ዝውውር አማካይነት የምንበላቸው ምግቦችና ኦክስጂን ከአንድ የኦርጋን ክፍል ውደሌላው በመሸጋገር ልዩ ልዩ ኦርጋኖች ተግባራቸውን እንዲያከናውኑ ይደረጋሉ። ልዩ ልዩ ኦርጋኖቻችንም አስፈላጊውን ተግባራቸውን የሚወጡት የማሰብ ኃይላቻንን በመጠቀምና ለሰውነታችንና ለማሰብ ኃይላችን ጠቃሚ የሚሆኑ ምግቦችን ስንመገብ ብቻ ነው። ከዚህ ቀላል አስተሳሰብ ስንነሳ አንድ ህብረተሰብና አገር ልክ እንደሰውነታችን በልዩ ልዩ ዐይነት የስራ-ክፍፍሎችና ተቋማት መያያዝና በየጊዜው መታደስ አለባቸው። ይህ ሲሆን ብቻ ነው አንድ ጤናማና ተከታታይነት የሚኖረው ማህበረሰብና ህብረተሰብ ለመገንባት የሚቻለው።

ይህ ዐይነቱ ከመንግስታዊ አወቃቀር ጀምሮ እስከ ኢኮኖሚ ፖሊሲውና በትምህርት አወቃቀር ላይ በተለይም የአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም የነበረው የረቀቀ  ተፅዕኖ በገጠር ውስጥ የሚታየውን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ግኑኝነትች ሊያሻሽለው አልቻለም። በተለይም ገበሬው በዝቅተኛ ቴክኖሎጂ እየታገዘ ያርስ ስለነበር ´እያደገ የመጣውን የህዝቡን የምግብ ፍላጎት ሊያሟላ አልቻለም። በአጠቃላይ ሲታይ ፊዩዳል በመባል የሚታወቀው የህብረተሰብ ክፍል በአንዳንድ የእርሻ መስኮች ላይ በመሰማራት እንደቡና የመሳሰሉትና ሌሎችም ምርቶች እንዲመረቱ ከማድረግ በስተቀር ወደ ተሻለ የአመራረት ስልት ሊሸጋገር በፍጹም አልቻለም። ስለሆነም በአገራችን ምድር የተዘበራረቁና ወደ ኋላ የቀረ የአኗኗር ስልት ዘመናዊ ከሚባለውና ይህን ያህልም ውስጣዊ ኃይል ከሌለው ጋር በመቆላለፍ ህብረተሰብአችን ወደ ተሻለ የአኗኗር ስልት ሊያሸጋግረው አልቻለም። ከተማዎችና መንደሮች ጥበባዊ በሆነ መንገድ ሊገነቡ በፍጹም አልቻሉም። በተለይም በክፍላተ-ሀገር ደረጃና በገጠር ውስጥ ያለውን የሰው ኃይልና የጥሬ-ሀብት ለማንቀሳቀስ የሚችል ዘመናዊና የሰለጠነ ተቋማት ባለመኖሩ ከ90% በላይ የሚሆነው ህዝባችን ካለምንም አጋርና ደጋፊ የሚኖር ነበር። ይህ ዐይነቱ የተዘበራረቀና ደካማ የኢኮኖሚ መዋቅር ሊዘረጋ የቻለው መንግስት የሚባለውና አገዛዙ ራሱ አገር በምን ዐይነት መሰረት ላይ በተከታታይነት መገንባት ይቻላል በሚለው ጉዳይ ላይ ይህን ያህልም በቂና ሳይንሳዊ ግንዛቤ ያላቸው ባለመሆናቸው ነው። በሌላ አነጋገር፣ ሰው ማለት ምን ማለት ነው? ህብረተሰብስ ማለት ምን ማለት ነው? እንዴትስ ነው አንድ ህብረተሰብና በራሱ የሚተማመን ህዝብ ሊገነባና ሊኮተኮት የሚችለው? የሚሉትን ጥያቄዎች ሊያነሳ የማይችል የህብረተሰብ ክፍልም ባለመኖሩ አገዛዙ ተግባራዊ ያደርጋቸው የነበሩ ፖሊሲዎች በሙሉ ከህብረተሰቡ ፍላጎትና ከጠቅላላው የአገራችን ዕድገት ጋር የተያያዙ አልነበሩም። ስለሆነም እንደዚህ ዐይነት በሳይንስና በፍልስፍና እየተመረመረና እየተፈተነ ተግባራዊ የማይሆን የኢኮኖሚ ፖሊሲ የግዴታ የተዘበራረቀ ሁኔታ መፍጠሩ የማይቀር ጉዳይ ነው። የመጨረሻ መጨረሻም የተራበና ድህነት የሚያጠቃው ህዝብ አገዛዙን ለመጋፈጥ ይገደዳል ማለት ነው።

ከዚህ ሁኔታ ስንነሳ በስድሳኛውና በሰባኛው ዓ.ም የተማሪው እንቅስቃሴ የኢትዮጵያ ህዝብ ጠላቶች፣ በመሰረቱ የዕድገት ጠንቆች ፊዩዳሊዝም፣ ቢሮክራሲያዊ ካፒታሊዝምና ኢምፔሪያሊዝም ናቸው ብሎ ሲነሳ  ትክክል ቢሆንም፣ በሌላ ወገን ደግሞ እያንዳንዱን ጽንሰ-ሃሳብ በተናጠል በመውሰድና ያላቸውን መተሳሰር አስመልክቶ ሰፋ ያለና የጠለቀ ጥናት ለማድረግ ባለመቻሉ ከሰከነ ትግል ይልቅ ወደመፈክሮች ጋጋታ ላይ ብቻ በማትኮሩ ነገሩ ሰፋ ያለ ግሽበት እንዲኖረው ለማድረግ በቃ። በዚህም ምክንያት የተነሳ አብዮቱ ሴፈነዳና ደርግም ስልጣንን ሲቀዳጅ ተመራምሮና አጥንቶ በዕምነት የወሰደው ፀረ-ኢምፔሪያሊስት ትግል ሳይሆን በጊዜው በነበረው ሁኔታ በመገፋት ብቻ ነው። አሁንም በሌላ አነጋገር፣ አብዛኛው በስልጣን ውስጥ የተካተተውና ስልጣንን የያዘው ደርግ የሚባለውና ሌሎችም የመንግስት መዋቅሮች ውስጥ ያሉ ኃይሎች በሙሉ  የአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም ተፅዕኖ ስለነበረባቸው ሙሉ በሙሉና አስተማማኝ በሆነና በጥናት ላየ በተመረኮዘ የአገር ወዳድነት ስሜት የአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝምንና የግብረ-አበሮቹን ልዩ ልዩ ሴራዎች ሊረዱና ሊዋጉ የሚችሉ አልነበሩም። እንዲህ ስል ግን ጠቅላላው በደርግ አገዛዝ ውስጥ የተካተተው ኃይልና በመንግስት መኪና ውስጥ የነበሩት የሲቪሊና የሚሊታሪ ቢሮክራቶች እንዳሉ የአገር ወዳድነት ስሜት አለነበራቸውም ማለቴ አይደለም። በሌላ ወገን ደግሞ በጊዜው ተራማጅ ወይም ግራ ነኝ በሚለው መሀከል የነበረው ቅራኔና የስልጣን ሽኩቻ ይህ በራሱ በደርግ ውስጥ አለመተማመንን ሊፈጥር ችሏል። በተለይም በአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም የተጠለፈው የተወሰነው የግራ እንቅስቃሴ መሪዎችና የነፃነትን አርማ ይዘው እዚህና እዚያ የሚንቀሳቀሱትና ውዥንብር የሚነዙት ኃይሎች ለደረግ አገዛዝ መደላደልን ሊሰጡት አልቻሉም። በተጨማሪም እንደ ኢህድ የመሳሰሉት ኋላ-ቀር አስተሳሰብ የነበራቸውና ከላይኛው የህብረተሰብ ክፍል የተውጣጡት ኃይሎች ራሳቸውን ለአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም በመሸጥና ኮሙኒዝምን እዋጋለሁ በማለት ያደረጉት አላስፈላጊና አላዋቂ እንቅስቃሴ ለደርግ አገዛዝ መደላደልን ሊስጠው በፍጹም አልቻለም።  እነዚህ ኃይሎች በሙሉ አሜሪካን የሚፈልገውን አገርን የማፈራረስ ተግባር በመፈጸማቸው የአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም ደርግን ሊያዳክም የሚችልበትን መንገድ በቀላሉ ለማግኘት ቻለ። ከዚህም በላይ የአንዳንድ የሚሊታሪና የሲቪል ቢሮክራቶች ስብስብና ኋላ-ቀር አመለካከት ያላቸው ኃይሎች፣ የኋላ ኋላ ከኮረኔል መንግስቱ ኃይለማርያም ጋር ቅራኔ ውስጥ ገብተናል ብለው ወደ አሜሪካን ሸሽተው የገቡት ኃይሎች ሁሉ በመሰረቱ ዲሞክራሲንና የተሻለ የዕድገት ስትራቴጂን በመፈለጋቸው ሳይሆን የአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም የሚፈልገውን ነገር ለመስራት ታጥቀው በመነሳታቸው ነው ቅራኔ ውስጥ ለመግባት የቻሉት።

በዚህም ምክንያት የተነሳ  በደርግ ውስጥና በተለይም ደግሞ በሚሊታሪ ውስጥ ያለውን ቅራኔ በማባባስ ወደ ውስጥ ስርዓት ያለውና በቲዎሪና በሳይንስ የሚደገፍ ትግል በፍጹም ማካሄድ አልተቻለም። መወያየትና ማጥናትም የሚቻልበት ጊዜ አልነበረም። ሁሉም በየፊናው ተነሰቶ ታጋይ ነኝ ይል ስለነበረና፣ ይህንንም ሆነ ያኛውን ኃይል ያግበሰብስ ስለነበር ይህ ዐይነቱ ሁኔታ ኃይልን የሚሰበስብ ከመሆኑ ይልቅ በታታኛ ለመሆን በቃ። አንደኛው ግራ ነኝ የሚል ድርጅት ሌላውን ያሳድደውና ይዝትበት ስለነበረና፣ አልፎ አልፎም “አደገኛ ናቸው የሚባሉትን” ለማስወገድ ኃይልን ይጠቀም ስለነበር በዚህ ዐይነት ሁኔታ ውስጥ የተሳካ ፀረ-ኢምፔሪያሊዝም ትግል ማካሄድ አይቻልም ነበር። ስለሆነም በዚህ ዐይነት በተዘበራረቀ ሁኔታ ውስጥና ኃይልን በተታኝ በሆነ የትግል ዘዴ ኢምፔሪያሊዝም ይውደም እያሉ መጮኹ የነበረውን ትርምስና ርስ በእርስ መጠፋፋት ሊያባብሰው ችሏል። የአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም የጂኦስታርቴጂ አርቃቂዎች እንደሚሉት በአሁኑ ጊዜ እኛ በቀጥታ ገብተን አንድን አገር መውረር አያስፈልገንም፣ ርስ በእርሱ የማይተማመን የህብረተሰብ ክፍል በመፍጠር እንዲጨራረሱ እናደርጋቸዋለን የሚለው አካሄዳቸው በእርግጥም በአገራችን ምድር ተግባራዊ ለመሆን በመቻሉ የመጨረሻ መጨረሻ አብዮቱ ሊከሽፍና የደርግ አገዛዝም ሊወድቅ ችሏል። ያ ብዙ የተወራለትና የብዙ መቶ ሺሆች ህይወት እንዲጠፋ የተደረገበት አብዮትም የመጨረሻ መጨረሻ ደብዛው ሊጠፋ ችሏል። በጊዜው ባለማወቅና ካለበቂ ዝግጅትና ምሁራዊ ጥልቀት የተካሄደው አላስፈላጊ መጨራረሽ ከሶሻሊዝም፣ ከማርኪስዝም ሌኒንዝምና ከግራ አስተሳሰብ ጋር ለመያያዝ  በመቻሉ ከዚያ በኋላና፤ በተለይም ደግሞ ወያኔ ስልጣንን ይዞ አገሪቱን ሲያተረማመስ አዲስና በሳይንስ ላይ የተመሰረተ የመታገያ መመሪያና መሰረት ለመጣል አልተቻለም። በተለይም ግሎባላይዜሽንን አሳቦ የተነዛው አሳሳች ቅስቀሳና ብልጭልጭ ሁኔታ ጊዜው ፀረ-ኢምፐሪያሊዝም ትግል የሚካሄድበት ሳይሆን ዓለም ወደ አንድ መንደር እያመራችና በየአገሮች ውስጥም የነፃ ገበያ ተግባራዊ የሚሆንበት ዘመን ነው የሚለው የተሳሳተ አስተሳሰብ ስልተነዛ የፀረ-ኢምፔሪያሊዝም ትግል ሳይሆን ቢያንስ ዲሞክራሲያዊና ትችታዊ አስተሳሰብን ሊያዳብር የሚችል ጥናትና ውይይት ማካሄድ በፍጹም አልተቻለም። ስለሆነም ባለፉት ሰላሳ ዓመታት ፀረ-ኢምፔሪያሊዝም ትግል ማካሄድ እንደ አረጀና አክራሪነት የሚወሰድበት ጊዜና፣ የድሮ ተራማጆች ነን ባዮችም በሙሉ ሳይቀሩ ከአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም ጎን በመሰለፍ ቢያንስ የዲሞክራሲያዊ ጥይቄዎችን በማንሳት በአስተማማኝ ሁኔታ ለሚገነባ ማህብረሰብ የሚታገሉትን ኢትዮጵያውያን ኃይሎች በሙሉ አክራሪና ግራ-ቀደም እያሉ የስም ማጥፋት ዘመቻ በማካሄድ የሰከነ ጥናት እንኳ ማካሄድ በፍጹም አልተቻለም።

በመሰረቱ አንድ የውጭ ኃይል አንድን ደካማ አገር ሲወር የሚደረገው ትግል ከፀረ-የቅኝ አገዛዝ ጋር የሚያያዝ ነው። በተለይም የቅኝ ግዛት-አስተሳሰብ ከተነሳበት ከአስራዘጠነኛው ክፍለ-ዘመንና አገሮችን እስከመውረር ያደረሰው የኤምፒሪያሊስት ኃይሎች አካሄድ ለፀረ-ቅኝ አገዛዝና ለፀረ-ኢምፔሪያሊዝም እንቅስቃሴ አመቺ ሁኔታን ሊፈጥር ችሏል።  ስለሆነም በጊዜው ይካሄድ የነበረው ትግል ፀረ-የቅኝ ግዛት ትግል ብቻ ሳይሆን ፀረ-ኢምፔሪያሊዝምም ነው። ምክንያቱም የቅኝ- አገዛዝ አስተሳሰብና ደካማ አገሮችን በዚህም በዚያም አሳቦ በመውረር ቀስ በቀስ እያለ በማደግ ላይ ያለውን ባህላዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ግኑኝነት ማዳከመና መበጣጠስ የግዴታ የሚያያዘው ከኢምፔሪያሊዝም ጋር ብቻ በመሆኑ ትግሉም በሁለቱም ላይ ያነጣጠረ ነበር ማለት ይቻላል። ቅኝ-ግዛት ከኢምፔሪያሊዝም ጋር የሚያያዝና የሱ ውጤትም በመሆኑ የተደረገውና የሚደረግው ትግል እዚያው በዚያው ፀረ-ቅኝ አገዛዝና ፀረ-ኢሞፔሪያሊዝም ነው። ከዚህ ሀቅ ስንነሳ አፄ ምኒልክና አርበኞቻቸው፣ በኋላ ደግሞ በሁለተኛው የጣሊያን ወረራ ጊዜ የተካሄደው ትግል፣ ትግሉ ነፃነትን በመፈለግና ለውጭ የወራሪ ኃይል አልንበረክክም በማለት ነው። አስቸጋሪውና፣ በተለያም ደግሞ የአፄ ምኒልክን የፀረ-ቅኝ አገዛዝ ትግል የሚያደንቁ ሰዎችን አመለካከት ስንሰማ በፀረ-የቅኝ አገዛዝና በፀረ-ኤምፔሪያሊዝም መሀከል ያለውን ዲያሌክቲካዊ ግኑኝነት የተረዱ አይመስሉም። ቅኝ-ግዛትን እታገላለህ፣ የአፄ ምኒልክንና የጀግኖቻቸውን ትግልና ጀግንነትም አደንቃለሁ፣ በሌላ ወገን ደግሞ የአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም  ነገር ሲነሳብኝ ቁርጠት ይይዘኛል የሚለው አነጋገር  የሚያረጋገጠው ብዙ ነገሮች ያልተገለጹን መሆናቸው ነው። በአንዳንድ አገሮች ውስጥ ለምሳሌ እንደቻይና በመሳሰሉት አገሮች ውስጥ ለምን የፀረ-ኢምፔሪያሊዝም ትግል ሊሳካና፣ ቻይና ዛሬ ወደ ኃያል መንግስትነት ለመሸጋገር ቻለች የሚለወን ጥያቄ ብናነሳና ብንመራመር ኖሮ ቀላል መልስ ማግኘት በቻልን ነበር። እንደሚታወቀው ቻይናዎች ከሶስት ሺህ ዓመታት በላይ የዘለቀ የዲናሲቲዎች አገዛዝና፣ ህዝብን በቢሮክራሲያዊ ኃይል በማንቀስቅቀስ ትላልቅ ፕሮጀክቶችን የመሰራትና የህዝቡን ስሜት ማዳበር ከፍተኛ ልምድና ባህል ነበራቸው። ይህም ማለት የቻይና ህዝብ ለብዙ ሺህ ዓመታት ያህል በተለያዩ ስራዎች በመሰማራት ወደ ውስጥ ውስጣዊ-ኃይል ያገኘና ራሱን ያዘጋጀ ስለነበር ይህንን የመሰለ የተደራጀ ህዝብ በአንድ መርሆና ዓላማ ስር ለማሰባሰብ፣ ለማደራጀትና የውጭ ወራሪ ኃይልን ለመወጋት ይቻላል ማለት ነው። በዚህ ላይ እየዳበረ የመጣው የኬራሚክና የሀር ልብስ ማምረት ኢንዱስትሪ፣ ከዚያም በኋላ ለጠብመንጃ የሚያገለግል እንደባሩድ የመሳሰሉትን ፈንጂዎች መስራትና ትልቁን ግንብ መገንባት የመሳሰሉት ነገሮች ቢያንስ ቢያንስ የአስተሳሰብን አንድነትና መንፈስ ሊሰጣቸው ችሏል ማለት ይቻላል። በ1911 ዓ.ም የሪፑቦሊክ ምስረታ ከከሸፈ በኋላ በ1920ዎቹ እነማኦሴቱንግ የማርኪስዝምን ቲዎሪ መሰረት አድርገው ትግል ሲጀምሩ በተለይም በገጠር ውስጥ ያለውን ህዝብ ማንቃት፣ ማደራጀትና ማስተባበር ይህን ያህልም ከባድ አልነበረም። ከዚያ በኋላ የጃፓን ኢምፔሪያሊስታዊ ኃይል ከወረራቸው በኋላ ትግላቸውን ስርዓት ባለው መልክ ለማካሄድና ወደሚፈልጉት  ውጤት ላይ ለመድረስ ይህንንም ያህል ከባድ አለነበረም። ባጭሩ ቻይናዎች ከእኛው ምሁራዊ ኃይልና ማህበረሰብ ጋር ሲወዳደሩ የተሻለ ዕውቀትና የመንፈስ ጥንካሬ ስለነበራቸው እርስ በራሳቸው ሳይሻኮቱ ወደሚፈልጉት ኔሽን ቢልዲንግ(Nation Building) ሂደት ሊሸጋገሩ ችለዋል። በ1949 ዓ.ም ነፃ ከወጡም በኋላ የተለያዩ የአገር ግንባታ ሞዴሎችን በመጠቀም የመጨረሻ መጨረሻ ቅልቅልና ጠንካራ የሆነ በቴክኖሎጂ ላይ የተመሰረተ ካፒታሊስታዊ ኢኮኖሚ በመገንባት በአጭር ጊዜ ውስጥ ሁለት ሶስተኛው የሚሆነውን ህዝብ ከድህነት ለማላቀቅ ችለዋል። በአሁኑ ወቅት በአንዳንድ ቴክኖሎጂዎች በዓለም አቀፍ ደረጃ ቀዳሚነትን በማግኘት፣ በነፃ የሚንቀስቀስና ራሱን የቻለ ኢኮኖሚ መገንባት ችለዋል። ይህ ዐይነቱ ራስን ለመቻል የተደረገውን ትግል ስንመለከት ቻይናዎች፣ ቀደም ብሎ ደግሞ ራሺያኖችና ጃፓኖች ኢምፔሪያሊዝም የሚለውን በአንድ አገር ውስጥ የተሟላ ዕድገት እንዳይኖር የሚቀናቀነውንና አፍኖ የሚይዘውን ስርዓት ጠንቅቀው በማወቃቸውና፣ ቀሰ በቀስ ተግባራዊ መሆን የሚገባውን ኢኮኖሚያዊ ግንባታ፣ ማህበራዊና የህብረተሰብ አደርጃጀትና ንቃተ-ህሊና አስፈላጊነት በመረዳታቸው ነው። የሰፊውን ህዝብ ንቃተ-ህሊና ለማዳበር ደግሞ የግዴታ ሰፊው ህዝብ ማንበብና መጻፍ እንዳለበት በመረዳታቸው በዚህ ላይ ተከታታይነት ያለው ስራ ለመስራት ችለዋል። የዚህ ሁሉ ውጤት በአንድ በኩል ወደ ውስጥ ጠንካራ ማህበረሰብ እንዲገነባ ሲያስችል፣ ወደ ውጭ ደግሞ በራሱ የሚተማመንና የዓለምን ፖለቲካ የተረዳ ምሁራዊና የተገለጸለት ኃይል ለማፍራት ችለዋል ማለት ይቻላል።

ወደ አገራችን ስንመጣ በእርግጥ በድሮው መልክ ፀረ-ኢምፔሪያሊዝም ትግል ማካሄድና ቅስቀሳም ማድረግ አሰፈላጊ አይደለም። የመፈክር ጋጋታም የትም አያደርሰንም። በእኛ መሀከል ያለው ትልቁ ችግር በልዩ ልዩ መልኮች የሚገለጸውን ኢምፔሪያሊዝም የሚለውን ፀንሰ-ሃሳብ ከሳይንስ አንፃር ለመረዳት አለመቻላችን ነው። ኢምፔሪያሊዝም የሚለው ፅንሰ-ሃሳብ የአሜሪካን ካፒታሊዝም ወይም ደግሞ የምዕራቡ ካፒታሊዝም ካደገ በኋላ የተፈጠረ አስተሳሰብ ሳይሆን፣ ለብዙ ሺህ ዓመታት ያለና እነ ፕሌቶን የመሳሰሉት ፈላስፋዎች የሚጠቀሙበት ፅንሰ-ሃሳብ ነበር። በጊዜው አንድን ኃይል ኢምፔሪሊስታዊ ብሎ መጥራት ፅንሰ-ሃሳቡ በቀጥታ ከወረራ ጋር ለመያያዝ በመቻሉ ነው። ይሁንና በታሪክ ውስጥ ብቅ ብቅ ያሉትን ኢምፔሪያሊስታዊ ኃይሎችን ስንመለከት፣ የአቴኑ ኢምፔሪያሊዝም፣ የፐረሺያው ኢምፔሪያሊዝምና የሮማውያን ኢምፔሪያሊያስት ኃይሎች፣ እነዚህ ኃይሎች በመሉ አንዳንድ አገሮችን ቢወሩም ስልጣኔን የሚያመጡ እንጂ ያለውን በመደምሰስ የራሳቸውን ለመትከል ብቻ አልነበረም። አካሄዳቸውም ጥሬ-ሀብትን ለመፈለግ ሳይሆን ግዛትን ለማስፋፋትና ለማስገበር ስለነበር የራሳቸውን ስልጣኔ ካለው ጋር በማውሃድ ለወረሯቸው አገሮች በሙሉ እስከተወሰነ ደረጃ ድረስ ውስጠ-ኃይል ሊሰጧቸው ችለዋል። በጊዜው የነበረው አስተሳስብ ከዛሬው ኢምፔሪያሊስታዊ አስተሳሰብ ጋር ሲወዳደር በብዙ ሚሊዮን ማይሎች ርቆ የሚገኝና የአንድን አገር ባህል የመደምሰስና እንዳለ አንድን አገር የማፈረካከስ ባህርይ አልነበረውም።

በአንፃሩ ከካፒታሊዝም አብራክ የተፈጠረውን ኢምፔሪያሊዝምን ስንመለከት ባለፈው ጸሁፌ ላይ ለማብራራት እንደሞከርኩት´ ስርዓቱ ከብዝበዛና ከማፈናቀል ጋር የተያያዘ ነው። ሌሎች አገሮችን በመውረርና የጥሬ-ሀብታቸውን በመዝረፍ ነው እየደለበ ለመምጣት የቻለው። በዚያው መጠንም ከትውልድ ወደትውልድ የተላለፉ የስራ-ክፍፍልንና ተቋማትን፣ እንዲሁም ልዩ ልዩ እሴቶችን በመደምሰስና የፕላንቴሽን ኢኮኖሚንና አንድ ወጥ (Mono Culture) ምርትን በማስፋፋት ነው ሀብትን ለማካበት የቻለው። የካፒታሊዝም መሰረት የተነጠፈው በማዕከለኛው ክፍለ-ዘመን ቢሆንም፣ ካፒታሊዝም ይህንን መሰረት በማድረግ ነው ከዝቅተኛ ወደከፍተኛ ዕድገት ሊሸጋገር የቻለው። በመሀከሉ ከ15ኛው ክፍለ-ዘመን ጀምሮ የተካሄደው ባህላዊ ለውጥ፣ የመጨረሻ መጨረሻ ኢንላይተንሜንት የሚባለው በ17ኛው ክፍለ-ዘመን ብቅ ያለው ምሁራዊ እንቅስቃሴ ቀስ በቀስ ለሳይንሳዊ ምርምር መንገዱን በማዘጋጀት ካፒታሊዝም ካለሳይንስና ካለቴክኖሎጂ ሊያድግና ሊዳብር እንደማይችል ግልጽ እየሆነ መጣ። ይሁንና ከጋሊሌዮ ጀምሮ እስከ ሬኔ ዴካ ድረስና፣ ኒውተንና ላይብኒዝ የመሳሰሉትን ሳንቲስቶችና ፈላስፋዎችን ስራ ስንመረምር በሳይንስ ላይ ምርምር ሲያደርጉና ለቴክኖሎጂ ዕድገትም አስፈላጊውን መሰረት ሲጥሉ አስተሳሰባቸውና አካሄዳቸው በሙሉ ካፒታሊዝም በዚህ መልክ ያድጋል ብለው በማሰባቸው ሳይሆን የሰውን ልጅ ከነበረበት የጨለማ አኗኗር በማላቀቅ ራሱን በማግኘትና የተፈጥሮን ምስጢር በመረዳት የተሻለ ኑሮና ማህበረሰብ ብቻ እንዲመሰረት ለማድረግ ነበር። የካፒታሊዝም አነሳስና የኢንዱስትሪ አብዮት መካሄድ ይህንን የእነ ጋሊሊዮን፣ የኒውተንና የላይብኒዝምን አስተሳሰብ በመጻረር ሳይንስንና ቴክኖሎጂን ለሰው ልጅ መጠቀሚያ ሳይሆን ተፈጥሮን መበዝበዢያና የሰውን ልጅ መቆጣጠሪያ በማድረግ የተወሳሰበና ግልጽ ያልሆነ ሁኔታ ሊፈጠር ቻለ። እነ ማርክስ ከመነሳታቸው በፊት ይህንን ገደብ ያጣ የተፈጥሮን ሁኔታ የሚያናጋና የተፈጥሮን ህግ ያልተከተለ ብዝበዛና፣ በኢንዱስትሪ አብዮት ምክንያት የተነሳ የተከሰተውን ህብረተሰብአዊና ተፈጥሮአዊ መናጋት ያጠኑና የተመለከቱ ሮማንቲክሶች በመባል የሚታወቁ ምሁራን  አንድ ህብረተሰብ በዚህ መልክ መገንባት እንደሌለበት ለማሳየት ሞክረዋል። ይህም የሚያረጋግጥው አንድ ነገር ተግባራዊ ሲደረግ በአውሮፓ የምሁራን ባህል ውስጥ አንዳንድ ምሁሮች ዝምብለው እንደማይመለክቱ ነው። ሁሉም ነገር ትችታዊ በሆነ መልክ መታየትና መገምገም አለበት የሚለው አካሄድ በተለይም መንግስታትን እስከተወሰነ ደርጃ ድረስ ለመቆጣጠር አስችሏል። በየጊዜው ጥልቀትን እያገኘ የመጣው ትችታዊ ምሁራዊ እንቅስቃሴ፣ በተለይም እንደሶስይሎጂና የህሊና-ሳይንስ ምርምሮች፣ እንዲሁም ከእነ አዳም ስሚዝ በተለየ መልክ የፈለቀውና የዳበረው ብሄራዊ እኮኖሚ ወይም ደግሞ የኢኮኖሚን ዕድገት ከታሪክ ጋር ማያያዝና (Historical School) የኢኮኖሚ ዕድገትም ካለማኑፋክቸር ሊያድግና ውስጣዊ ኃይል ሊያገኝ አይችልም የሚለው  አስተሳሰብ የሚያረጋግጠው የአውሮፓ ምሁራን አንድን ነገር በጭፍን ዝምብለው እንደማይከተሉ ነው።

ያም ሆነ ይህ የካፒታሊዝም ዕድገት ለአዳዲስ አስተሳሰቦች መፀነስ ዕድል ቢሰጥም እንደፋሺዝምና ዘረኝነት የመሳሰሉት ርዕዮተ-ዓለሞች የፈለቁት ከዚህ ስርዓት ውስጥ ነው። ካፒታሊዝምም ከነጭ “ዘር” ጋር በግዴታ የሚያያዝ በመሆኑ፣ በተለይም ዘረኝነትን አጥብቀው ለሚሰብኩ ኃይሎች  ዕውቅና (Legitimacy) ሊሰጣቸው ችሏል። ከነጭ ዘር በስተቀር ሌላ የሰው ልጅ የሳይንስና የቴክኖሎጂ ባለቤት ሊሆን አይችልም፤ በአፈጣጠሩም ለሳይንስና ለቴክኖሎጂ የሚያመች አይደለም የሚለው አስተሳሰብ በዓለም አቀፍ ደረጃ በመስፋፋቱ ሁላችንም ሰጋጅና ነጭን አምላኪ ለመሆን በቅተናል። አንዳንዶቻችንም ጥቁር ወይም ቡናማ የመሰለውን ቀለማችንን በመጥላት ነጭ ፀጉርና ሰማያዊ ዐይን(Blond Hair and Blue Eyes) ያለውን የነጭ ዘር አምላኪ በመሆን ወደ አገር አፍራሽነት ለማምራት ችለናል።  በየቤተክርስቲያናትም ውስጥ የሚታዩት ስዕሎች፣ እየሱስንና ማርያምን ከነጭ ዘር ጋር ማያያዝ፣ ጥቁሩን ደግሞ ሰይጣን አስመስሎ ከስሩ ማስቀመጥ፣ እነዚህና ሌሎች ነገሮች በሙሉ ሳንወድ በግድ የነጭ ዘርን የበላይነት አሜን ብለን እንድንቀበል አስገድዶናል። ቀደም ብሎ በህወሃት የአገዛዝ ዘመን፣ አሁን ደግሞ በአቢይ የአገዛዝ ዘመን ነጮች ልዩ ቦታ የሚሰጣቸውና፣ ከውጭ ሃገር ወደ ኢትዮጵያ የሚመጡ ነጮች ልዩ  እንክብካቤ የሚደረግላቸውና ካለምንም ጥበቃና መንገላታት ከአውሮፕላን ማረፊያ ወርደው ወደ መሀል ከተማ ለመግባት እንደሚችሉ ነው የምንሰማው። በአንፃሩ ከውጭ ሀገር የሚገቡ ኢትዮጵያውያንም ሆነ ሌሎች የአፍሪካ አገር ዜጎች እውሮፕላን ጣቢያ ከደረሱ በኋላ ለማለፍ አራት ሰዓት ያህል እንደሚጠብቁ ነው የምንሰማው። በአንድ ስብሰባ ላይ አንድ የካሜሩን ሴት አዲስ አበባ አውሮፕላን ማረፊያ የደረሰባትን መንገላታት ስትነግረኝ እናንተ ኢትዮጵያውያኖች ዘረኞች ናችሁ በማለት ነው  ብሶቷን የነገረችኝ። ከኤርፖርቱ ውስት ለመውጣት አራት ሰዓት መጠበቅ እንደነበረባት እየተበሳጨች ነግራኛለች። እኔም ይህ ዐይነቱ ዘረኝነት አንቺን ብቻ ሳይሆን እኛ ኢትዮጵያውኖችንም የሚመለከት ጉዳይ ስለሆነ ጉዳዩ ከዕውቀትና ከንቃተ-ህሊና ማነስ ጋር እንደሚያያዝ በማስረዳት ላቀዘቅዛት ችያለሁ። ይህ ሁሉ የሚያረጋግጠው በተለይም የብሄረሰብን አርማ ይዘው ስልጣን ላይ የወጡና የሚወጡ የዚህም ሆነ የዚያኛው ብሄረሰብ ኤሊቶች ስልጣን ላይ ለመቆየት የሚችሉት ከውስጥ ዘረኝነትን ሲያስፋፉና ለነጩ ደግሞ ተገዢ ሲሆኑ ብቻ ነው።  ይህንንም ተገን በማድረግ ነው በተለይም እንደአሜሪካን የመሰለው ኢምፔሪያሊስታዊ ኃይል በእኛና በተቀረው ዓለም ህዝብ ላይ የበላይነቱ ለማስፈንና እንድናመልከውም ሊያደርገን የቻለው።

ለዚህ ደግሞ በተለይም ከሁለተኛው ዓለም ጦርነት በኋላ የተፈጠረው አዲስ የኃይል አሰላለፍና፣ የአሜሪካን ዶላርም የዓለም የመገበያያና ማስቀመጫ መሳሪያ(Trading and Reserve Currency)1 መሆን የአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም ዶላርን በመጠቀም በተለይም የአፍሪካን ዕድገት መቆጣጠሪያና ሀብቷን መበዝበዢያ መሳሪያ ለማድረግ በቅቷል። በተለይም የዓለም አቀፍን ስም የተከናነቡ፣ እንደ ዓለም አቀፍ የገንዘብ ድርጅትና(IMF) የዓለም ባንክ(World Bank) የመሳሰሉትን ተገን በማድረግና ሳይንሳዊ ይዘት የሌለው፣ አንጀት አጥብቅ የኢኮኖሚ ፖሊሲ(Austerity Economic Policy) ተግባራዊ እንዲያደርጉ በማስገደድ በየአገሮቹ ውስጥ ያልተስተካከለ ሁኔታ (Unbalanced Situation) እንዲፈጠር ለማድረግ ቻለ። በተለይም እያንዳንዱ አገር የማክሮ ኢኮኖሚ ፖሊሲ(Macroeconomic Policy) ተግባራዊ ማድረግ አለበት በማለት ከየአገሩ ተጨባጭ ሁኔታና ከህዝቡ ፍላጎት ውጭ የሆነ የኢኮኖሚ  ፖሊሲ እንዲተገበር በማድረግ ድህነትና ረሃብ እንዳይወገዱ ለማድረግ በቃ። ይህ ዐይነቱ የማክሮ ኢኮኖሚክ ፖሊሲ ደግሞ ሙሉ በሙሉ በነጻ ገበያ ላይ የሚመረኮዝና የመንግስትን ጣልቃ-ገብነት የሚቃወም በመሆኑ ፖሊሲው ሁለ-ገብ ከመሆን ይልቅ በተናጠል ነገሮች ላይ ብቻ የሚያተኩር ለመሆን በቃ። በእነ ዓለም የገንዘብ ድርጅትና በዓለም ባንክ፣ በአጭሩ በዓለም አቀፍ ኮሙኒቲው የሚደነገገው የማክሮ ኢኮኖሚክ ፖሊሲ ደግሞ በመሰረቱ በታላቁ ኢኮኖሚስት በኬይንስ የረቀቀውንና አብዛኛዎቹ የካፒታሊስት አገሮች ከሁለተኛው ዓለም ጦርነት በኋላ ተግባራዊ´ ያደረጉትን በመንግስታጥ ጣልቃ-ገብነት የተደገፈውን የመልሶ ግንባታ ፖሊሲ እንዳለ የሚፃረር  ነው። በኬይንስ ዕምነትም የካፒታሊስት ኢኮኖሚ ዕድገት በየጊዜው ከፍና ዝቅ ስለሚልና፣ በዚህም የተነሳ የስራ-አጥ ቁጥር ስለሚጨምር የግዴታ መንግስት በፊስካል ፖሊሲ አማካይነት ጣልቃ በመግባት ኢኮኖሚው እንዲንቀሳቀስ ማድረግ መቻል አለበት። መንግስት ራሱ እንደጠያቂ ስለሚቀርብና ለልዩ የግል ተቋራጮች ኢንቬስት እንዲያደርጉ ዕድል ስለሚሰጥ በዚያው መጠንም ገንዘብ በቀጥታ ወደምርታማ ነገሮች ላይ በመፍሰስ ኢኮኖሚው እንዲያድግ ያደርጋል ይላላ። ስለሆነም በዚህ መልክ በተዘዋዋሪ የሚደጎመውና የሚታገዘው ኢኮኖሚ የስራ መስክ በመክፈት የሚመረቱት ምርቶች በመሸጥ፣ በተዘዋዋሪ ደግሞ በኢኮኖሚው ማደግ የተነሳ የመንግስትም የቀረጥ መሰረት(Tax Base) በማደግ በየጊዜው ከቀረጥ ስብሰባ የሚያገኘው ገቢ ስለሚጭምር ዕዳውን ለመክፈልና የተቀረውን ደግሞ መልሶ ለመዋዕለ-ነዋይ እንዲያውለው ዕድል ያገኛል ይላል። ይህንን የኬይንስን ቅዱስና ትክክለኛ አመለካከትና አካሄድ የዓለም አቀፍ የገንዘብ ድርጅትና የዓለም ባንክ፣ ባጭሩ ኒዎ-ሊበራል የሚባሉት ኢኮኖሚስቶች እንዳለ ይቃወሙታል። በእነሱ ዕምነት ሁሉም ነገር ለገበያው መለቀቅ አለበት። ከረጅም ጊዜ አንፃር ገበያ ራሱን በራሱ የማረም ኃይል ስላለው ሁሉም ነገር ሚዛናዊነትን ያገኛል ይላሉ። በኢኮኖሚ ዕድገት ታሪክ ውስጥ ያልታየ ነገር በመንዛት ብዙ ወጣት ተማሪዎችን ያሳስታሉ ማለት ነው።

ለማንኛውም  የአሜሪካን ዶላር ከወርቅ ከተነጠለ  ከ1971 ዓ.ም በኋላና፣  በ1973  ዓ.ም ከቋሚ የገንዘብ ልውውጥ(Fixed Exchange Rate) ይልቅ ተለዋዋጭ የገንዘብ ልውውጥ (Varaibale Exchange Rate)2 በተለይም በካፒታሊስት አገሮች ውስጥ ተግባራዊ እንዲሆን ሲወሰን፣ ከዘይት መወደድ ጋር በመደመር በዓለም አቀፍ ደረጃ የፋይናንስ ካፒታል ብቻውን ተለይቶ እንዲወጣ አደረገው። በዘይት ሺያጭ የተነሳ በዶላር የደለቡ አገሮች ገንዘባቸውን ወደ አውሮፓና አሜሪካ በማሸሽና ባንኮችን በማበልጸግ ለፋይናንስ ካፒታሊዝም ዕድገት  ልዩ ዕምርታን ሊሰጠው ቻለ። በዚህ ላይ ልዩ ልዩ የገንዘብ ማስቀማጫ ዘዴዎች፣ ሀብት መፍጠሪያና መበዝበዢያ መሳሪያዎች እንደ ሄጅ ፈንድስ(Hedge Funds)3 የመሳሰሉት በመፈጠራቸው በአፍሪካና በተቀሩት የሶስተኛው ዓለም አገሮች የሚገኙትን የጥሬ-ሀብቶች ለመቆጣጠርና ለመበዝበዝ አመቺ ሁኔታ ተፈጠረ።  በዚያው መጠንም በተለይም ከጥሬ-ሀብት መቆጣጠርና ማውጣት ጋር የተያያዙና በአሜሪካን ትላልቅ ኩባንያዎች የሚደገፉ ጦርነቶች(Proxy Wars) በመስፋፋትና ከየአገሩ አገዛዞች ጋር በመመሰጣጠር  ምስኪኑን ህዝብ መቆሚያ መቀመጫ ሊያሳጡት ቻሉ። በየአገሮች ውስጥም ዶላር ከመስፋፋቱ የተነሳ የአብዛኛዎቹ የሶስተኛው ዓለም አገር ኢኮኖሚዎች በዶላር ላይ የሚመኩ በመሆን፣ በየጊዜው በሚካሄደው የገንዘብ ቅነሳ(Devalutaion) ምክንያት የተነሳ የየአገሩ ገንዘብ የመግዛት ኃይል በከፍተኛ ደረጃ እንዲዳከም ለመደረግ በቃ። ካለ ዶላርና ኦይሮ ኢኮኖሚን ማሳደግ አይቻልም የሚለው ፍልስፍና ስለተስፋፋ የየአገሩ ገንዘብ ሊኖረው የሚችለውን ሚናና ኃይል ተፈላጊ ቦታ ሳይሰጠው ቀረ። በንግድ ልውውጥና በብድር አማካይነት ከውጭ የሚመጣው ዶላር ደግሞ አብዛኛው ምርትን ለማሳደግና(Productivity)  ለቴክኖሎጂያዊ ለውጥ ሳይሆን  ለቅንጦት ዕቃዎች ስለሚውል የውጭ ዕዳው በየዓመቱ እያደገና የንግድ ሚዛኑም በከፍተኛ ደረጃ እየተዳከመ ለመምጣት ቻለ። በዚህ መልክ ግሎባል ካፒታሊዝምና የአሜሪካን ዶላር ልዩ ቦታን መያዝና እንደአምልኮ መታየት በየአገሩ የሚገኘውን የጥሬ-ሀብትና የሰው ኃይል ስርዓት ባለው መልክ ማንቀሳቀስና ኢኮኖሚውን በሚያስተማምን መልክ መገንባት አልተቻለም። ባለፈው ጽሁፌ ለማሳየት እንደሞከርኩት በዚህ መልክ የሚገለጸው ካፒታሊዝም በየአገሮች ውስጥና በዓለም አቀፍ ደረጃ አመጽን በማስፋፋት፣ በተለይም በደካማው የህብረተሰብ ክፍል ዘንድ ፍርሃትን ማሳደር ቻለ። ካፒታሊዝም ባህላዊ ነገሮች የሚባሉትን የአሰራርና ስልቶችንና እሴቶችን በመደምሰስ የሰው አስተሳሰብ እንዳለ ወደ ፍጆታ አጠቃቀም( Consumption Pattern) እንዲለወጥ በማድረግ  የሰው የእርስ በርስ ግኑኝነትም በገንዘብ እንዲለካ ለማድረግ በቃ።  ሁሉም ነገር ገደብ እንዳይኖረው በማድረግ፣ በየአገሮች ውስጥ  ባህለ-አልባ አሰተሳሰብ መፍጠር ተቻለ። ካለገደብ መብላት፣ ካለገደብ መጠጣት፣ ካለገደብ ሁሉንም ነገር መመኘት፣ማግበስበስና ማድረግ የሚለው  አስተሳሰብ ስለተስፋፋ በተፈጥሮና በህብረተሰብ፣ እንዲሁም በባህል ላይ ከፍተኛ ዘመቻ በማካሄድ እንደኛ የመሰሉ አገሮች ትርምስ ውስጥ ሊገቡ ቻሉ። የአገራችን ተጨባጭ ሁኔታ ይህንን ነው የሚያረጋግጠው። በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ በመንገድ ላይ የሚሽከረከሩትን የቅንጦት መኪናዎችን ለተመለከተ፣ በጋብቻ ጊዜ በአምስት ኮከብ ሆቴልቤቶች ውስጥ የሚደገሰው ድግስና፣ ሙሽሮች የሚሄዱበት ከአሜሪካን የመጣ ርዝመቱ አራት ሜትር የሚያክል ነጭ መኪናና፣ በአንዳንድ ቦታዎች የሚሰሩት የገበያ አዳራሾችና(Malls) ለሺያጭ የሚደረደሩት የቅንጦች ዕቃዎች የሚያረጋግጡት የባህል ውድቀትን ነው። ይህ ዐይነቱ የፍጆታ አጠቃቀምና ልዩ ዐይነት መኪናዎች መሽከርከር ከአገራችን ተጨባች ሁኔታ ጋር የሚሄዱ አይደሉም። በተለይም ገንዘብ ይናገራል፣ ገንዘብ ዓለምን ያሽከረክራል(Money Talks and Money makes the World go round) የሚለው አስተሳሰብ በመስፋፋቱ የሰው ልጅ ህይወት ከመንፈሳዊ ይልቅ ይበልጥ ማቴሪያላዊ ለመሆን በቅቷል። እንደኛ ባለው ከፍተኛ ምሁራዊ ድክመት በሚታይበት አገር ውስጥ በየጊዜው ተግባራዊ የሚሆኑ የኢኮኖሚ ፖሊሲዎችን ለመመርመር ስለማይቻልና ፍላጎትም ስለሌለ እንደምናየው የአገራችን እሴትች በመበጣጠስ ሰፊው ህዝብ ግራ ተጋብቶ ይገኛል። ከፍተኛ የመንፈስ መቃወስም ይታያል። በአሁኑ ጊዜ ወደ ዕብድነት የሚጠጉ  17 ሚሊዮን የሚሆኑ ዜጎች በጭንቅላት ህመም እንደሚሰቃዩ ይነገራል።

ይሁንና ካፒታሊዝም እንደዚህ ዐይነት ብዝበዛ፣ ህብረተሰብአዊና ተፈጥሮአዊ ቀውስ ቢያስከትልም፣ በሌላ ወገን ግን በካፒታሊዝም አማካይነት ብቻ ነው ይህ ዐይነቱ የሳይንስና የቴክኖሎጂ ምጥቀት ሊታይ የቻለው። የባቡር ሃዲድ መፈጠርና በየጊዜው መሻሻል፣ አውሮፕላን ተፈጥሮና ተሻሽሎ ብዙ ወራቶችን የሜፈጀው መንገድ ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ በስምንት ሰዓታትና ከዚያም በታች ለመድረስ መቻል፣ በኢንተርኔት ቴክኖሎጂ አማካይነት መረጃዎችን ማግኘትና መለዋወጥ፣ ወንዝ ሄዶ ልብስ ከማጠብ ይልቅ በልብስ ማጠቢያ ቤት ውስጥ ማጠብና ማድረቅ... ወዘተ. እነዚህ ለውጦችና መሻሻሎች በሙሉ የሚያያዙት ከካፒታሊዝም ዕድገትና፣ ካፒታሊዝም ትርፍን ለማካበትና ገበያዎችን ለመቆጣጠር ሲል በሚፈጥረው አዳዲስ ቴክኖሎጂዎች የተነሳ ነው። ከዚህም በላይ ለሙዚቃና ለፊልም ኢንዱስትሪ አመቺ ሁኔታ በመፈጠሩ ሙዚቃና ፊልም፣ እንዲሁም ቲያትርና ልዩ ልዩ ሞዶች ዓለም አቀፋዊ ባህርይ በመውሰድ እስከተወሰነ ደረጃ ለመኮረጅ ተቻለ።  ሰለሆነም በካፒታሊስት አገሮች የተፈጠረው ቲክኖሎጂ  እስከተወሰነ ደረጃ ድረስ የዓለም ህዝብ ሊጠቅምበት ችሏል ማለት ይቻላል። ይህ ዐይነቱ የሳይንስና የቴክኖሎጂ ጠቀሜታ ግን የዓለምን ህዝብ እንዳለ ውስጣዊ ኃይል(Empower) ሊያጎናጽፈው አልቻለም። ቀደም ብዬ ባብራሁት ምክንያት የተነሳና፣ ካፒታሊዝምና ኢምፔሪያሊዝም ልዩ መስመርን ለመከተል በመቻላቸው፣ የስውን ልጅ ነፃነት የመቀናቀንና ውስጠ-ኃይሉን የማዳከም ኃይላቸው እያየለ ለመምጣት ችሏል። በአብዛኛዎቹ የሶስተኛው ዓለም አገሮች የሚገኙት አገዛዞች የሳይንስና የቴክኖሎጂን ምንነት ባለመረዳታቸው ከኢምፔሪያሊዝም ጋር በመቆላለፍ ይበልጥ ጨቋኞች ለመሆን በቁ። በዚህ አካሄዳቸው የሰውን ልጅ ውስጣዊ ኃይልና ፍላጎት በማፈን እንዳለ ነፃነቱን ለመግፈፍ በቁ።

ከዚህ ዐይነቱ አጠቃላይ ሁኔታ ስንነሳ በዛሬው መልክ የሚካሄደው ትግል የሳይንስን ምንነትና ሚና፣ በተለይም ደግሞ የተለያዩ የኢኮኖሚና የህብረተሰብ ሳይንስ ቲዎሪዎችን በማጥናትና በመረዳት ለአገራችን የተሟላ ዕድገት የሚያመቸውን መስመር መከተል ነው። ከዚህም በላይ አንድ አገር የተሟላ ዕድገት ለማግኘት የምትችለውና ህዝቡም ዕውነተኛ ነፃነት የሚሰማው ኢኮኖሚክስ ከተፈጥሮ ሳይንስ፣ በተለይም ከፊዝክስ ጋር የተያያዘ ሲሆን ብቻ ነው። ኢኮኖሚ ቲዎሪና ፖሊሲ በራሳቸው ምንም ነገር  ሊፈጥሩ የሚችሉት ነገር የለም። በኃይልና(Energy)
https://amharic-zehabesha.com/archives/177933

No comments:

Post a Comment

https://youtu.be/VUfa5eupQTc?si=Zm73w18dFB27xlqD       https://youtu.be/LcFmz2Xq5MY?si=7uP6VZsd2ksEulUf   https://youtu.be/7dUVmj8go7s?si=Px...